ማዕከሉ እንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በስፋት እና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ ነው

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 10/2017(ኢዜአ)፦ለትንሳኤ በዓል እንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በስፋት እና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ እንደሚገኝ የአዲስ አበባ ከተማ አርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን አስታወቀ።

የአዲስ አበባ ከተማ አርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽነር ባዩ ሽጉጤ እንደገለጹት፤ በኮሚሽኑ ሥር ባለው የእንስሳት ልማትና ልህቀት ማዕከል አማካኝነት መጪውን የትንሳኤ በዓል ምክንያት በማድረግ ለህብረተሰቡ የተለያዩ የእንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በተለያዩ የገበያ ማዕከላት በመሸጥ ላይ ይገኛል።


 

በተለይም ማዕከሉ ህብረተሰቡ ለበዓሉ የሚፈልጓቸውን የእንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በስፋት  እና በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት እንዲችል እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

ለህብረተሰቡም እየቀረቡ ካሉት ውስጥ የእርድ እንስሳት እና የእንስሳት ተዋጽኦዎች መካከል ዶሮ፣ ሰንጋ በሬዎች እና እንቁላል ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልጸዋል። 


 

በመዲናዋ 117 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ላይ ከ451 ሺህ በላይ ዶሮዎች እና ከአምስት ነጥብ ዘጠኝ ሚሊዮን በላይ እንቁላል ለገበያ እየቀረበ መሆኑን ገልጸው፤ በቀጣይም አቅርቦቱ እያደገ እንደሚሄድ አብራርተዋል።


 

በማዕከሉ እንደየመጠናቸው ከ80ሺህ ብር ጀምሮ ሰንጋዎች ለገበያ አቅርቦ እየሸጠ መሆኑን ጠቁመዋል።

ሴቶች አደባባይ አካባቢ በሚገኘው የእንስሳት ልማትና ልህቀት ማዕከል የመሸጫ ቦታ ላይ የእንስሳት ተዋጽኦ  ምርቶች በመሸጥ ላይ መሆኑን ኢዜአ ለመመልከት ችሏል።


 

አቶ ፀጋዬ ጎብዴ ለአካባቢው ነዋሪዎች በዓሉን ምክንያት በማድረግ ከማዕከሉ  እንቁላል በመሸጥ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።   

እንቁላል ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል።


 

የእንስሳት ተዋጽኦ ውስጥ ቅቤ በ800 ብር፣ አይብ 400 እና ወተት በሊትር 80 ብር ለገበያ አቅርበናል ያሉት ደግሞ ወይዘሮ የሺወርቅ ዳኛቸው ናቸው።

ለበዓሉ እንቁላል ሲገበዩ ካገኘናቸው የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል ወይዘሮ አስቴር አበበ እና ወይዘሮ  አስካለ ትኩ በሰጡት አስተያየት ከማዕከሉ በተመጣጣኝ  ዋጋ እየሸመቱ መሆናቸውን ተናግረዋል።


 

በዚህም አንድ እንቁላል በ10 ብር ሂሳብ መግዛታቸውን ተናግረው፤ ይህም ከሌላው ቦታ ዋጋው ቅናሽ ያለው ነው ብለዋል።

በቀጣይም ህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ የተለያዩ የግብርና ምርቶችን እንዲገበያይ ተመሳሳይ ማዕከላት ሊጠናከሩ እንደሚገባ ጠይቀዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም