በጉራጌ ዞን በበጋ መስኖ ከለማው መሬት ከ5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል - መምሪያው

ወልቂጤ፤ ሚያዚያ 5/2017(ኢዜአ)፦ በጉራጌ ዞን ዘንድሮ በበጋ መስኖ ከለማው መሬት እስካሁን ድረስ ከ5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ።

የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በዞኑ በበጋ መስኖ 25ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን ተናግረዋል።

ከዚህም ከ6 ሚሊዮን በላይ ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ እስካሁን ድረስ ከ5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ መሰብሰቡን ጠቁመዋል።

በዞኑ በመስኖ ልማት በቆሎ እና ድንች ማልማት እምብዛም የተለመደ አይደለም ያሉት አቶ አበራ፣ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ግን ከፍራፍሬና አትክልት ልማት ቀጥሎ በቆሎና ድንች በመስኖ ማልማት እየተለመደ መምጣቱን ገልጸዋል።


 

ምርታማነትን ለማሳደግም ሳይታረሱ የኖሩ እና ባህር ዛፍ የነበረባቸውን መሬቶች ዛፉን አንስቶ በማልማት የአርሶ አደሩንና የወጣቱን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑንም አስረድተዋል።

የአትክልትና ፍራፍሬ ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ በወቅቱ ግብአት ከማቅረብ ባለፈ በግብርና ባለሙያዎች ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

በበጋ መስኖ ልማት ሥራ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል በዞኑ የእኖር ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር ደሊል ሸምሱ እንዳሉት በመስኖ የተለያዩ አትክልቶች፣ ፍራፍሬና ሰብል ልማት እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል።

በመጀመሪያ ዙር የመስኖ ልማት ሽያጭ ከ300ሺህ ብር በላይ ገቢ ማገኘታቸውን ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት በሁለተኛ ዙር መስኖ ያለሙት አትክልት ለሽያጭ መድረሱን ተናግረዋል።


 

ሌላው በወረዳው በግብርና ኢንቨስትመንት የተሰማሩት አቶ አሚኑ ነጂሙ በበኩላቸው፣ በመስኖ ካለሙት የአትክልትና የሰብል ምርት ውጤት ማግኘታቸውን አስታውቀዋል።

በዞኑ ቸሃ ወረዳ የባህር ዛፍ ተክልን በማንሳት በሁለት ሄክታር ማሳ ላይ ዝንጅብል፣ አቮካዶና የተለያዩ ሰብሎችን የሚያለሙት አርሶ አደር አዳነ ሹሜም እንዲሁ ከልማቱ ከ500ሺህ ብር በላይ ትርፍ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም