ቀጥታ፡

ኢትዮጵያን ጨምሮ በሰባት የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከመደበኛው በላይ ዝናብ ይጠበቃል

ኢትዮጵያን ጨምሮ በሰባት የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከመደበኛው በላይ ዝናብ የሚጠበቅ መሆኑን የምስራቅ አፍሪካ የአየር ሁኔታ መረጃ አገልግሎት (ኢክፓክ) አስታወቀ።

የኢክፓክ የቀጣዮቹ ስምንት ቀናት የአየር ትንበያ መረጃ እንደሚያመለክተው በምስራቅ አፍሪካ አገራት ከመደበኛው በላይ፣ መጠነኛ እና ዝቅተኛ የዝናብ ስርጭት የሚኖር ይሆናል።

በዚህም መሰረት የዝናብ ስርጭቱ በደቡብና ማእከላዊ ኢትዮጵያ፣ደቡብ ሱዳን፣ኡጋንዳ፣ሩዋንዳ፣ ብሩንዲ፣የታንዛኒያ ምእራባዊ ክፍል፣በኬኒያ በርካታ አካባቢዎች እና በሶማሊያ ደቡባዊ ክፍል ከመደበኛው ከፍ ያለ ዝናብ ይኖራል።

በታንዛኒያ አብዛኛው አካባቢዎች፣ሶማሊያ፣ጅቡቲ እና ኤርትራ፣ በኬኒያ ምስራቃዊ ክፍል፣ በደቡብ ሱዳን እና የሶማሊያ ደቡባዊ ክፍል ከፍተኛ የሙቀት መጠን እንደሚኖር ይጠበቃል።

በመሆኑም በእነዚህ አካባቢዎች የጎርፍ አደጋ ሊከሰት ስለሚችል ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት አመላክቷል።

የምስራቅ አፍሪካ የአየር ሁኔታ መረጃ አገልግሎት (ICPAC) በኢጋድ ስር ሆኖ የአየር ትንበያና ሌሎች ተያያዥ ተግባራትን የሚያከናውን ቀጣናዊ ተቋም መሆኑ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም