የአዳማ ከተማ የካዳስተር የመሬት አስተዳደር ስርዓት በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የአዳማ ከተማ የካዳስተር የመሬት አስተዳደር ስርዓት በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ ነው

አዳማ ፤መጋቢት 29/2017 (ኢዜአ) ፡-የአዳማ ከተማ የካዳስተር የመሬት አስተዳደር ስርዓት በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑ ተገለጸ።
በአዳማ ከተማ 117 ሺህ የመሬት ይዞታ ፋይሎች ወደ ካዳስተር እንዲገቡ መደረጉን የከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል።
ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የከተማ ልማትና መሬት ቢሮ የተወጣጣ ቡድን የአዳማ ከተማን የመሬት አስተዳደር የዲጂታል አሰራርና ካዳስተር አገልግሎት በተመለከተ ልምድ ተጋርቷል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ምክትል ሃላፊ ዝናቡ ተካበ፤ በአዳማ ከተማ የመሬት ሀብት አስተዳደርና አገልግሎቶች አሰጣጥ ዘመኑን የዋጀ መሆኑን ገልፀዋል።
በተለይ የመሬት ሀብቱን በአግባቡ ለማስተዳደርና ለመጠቀም የተጀመረው የካዳስተር ስራ የሚደነቅና በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑን ተናግረዋል።
ከአዳማ ቆይታቸው በአገልገሎት አሰጣጥ የመሬት ማኔጅመንትና ተያያዥ ጉዳዮችን በመጎብኘት ጠቃሚ ልምዶችና አሰራሮችን በመቅሰም በከተሞቻቸው ለመተግበር መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ፤ በከተማዋ የመሬት ሀብትን በአግባቡ ለማስተዳደር፣ ለማልማትና ለመጠቀም የዲጂታል አገልግሎት ተዘርግቶ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
በካዳስተር አሰራር ከሊዝ አዋጅ በፊት የተገነቡ ሰነድ አልባ ቤቶች ወደ ህጋዊ ስርአት እዲገቡ እንዲሁም 117 ሺህ የመሬት ይዞታ ፋይሎች ወደ ካዳስተር እንዲገቡ መደረጉንም ተናግረዋል።
በህገ ወጥ መንገድ ተይዞ የነበረ በድምሩ ከ200 ሄክታር በላይ መሬት ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ መደረጉን ጠቅሰው ግልጽ አሰራርና ተጠያቂነትን በማስፈን የዘርፉን ገቢ ከማሳደግ ባለፈ ብልሹ አሰራርን መከላከል መቻሉን ጠቅሰዋል።
ከሊዝ አዋጅ በፊት የነበሩ ሰነድ አልባ ይዞታዎችን ወደ ህጋዊ መስመር ለማስገባት የተደረገው ጥረት ስኬታማ መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህ ሂደት አሰራሩን ህጋዊ ከማድረግም ባለፈ ከ610 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል ።