ስማርት ሲቲ ግንባታን ለማሳለጥ የተቋማትን አሰራር ቴክኖሎጂ መር እየተደረገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ስማርት ሲቲ ግንባታን ለማሳለጥ የተቋማትን አሰራር ቴክኖሎጂ መር እየተደረገ ነው

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማን የስማርት ሲቲ ጉዞ ለማሳለጥ የተቋማትን አሰራር ቴክኖሎጂ መር የማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የከተማዋ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ አስታወቀ።
የአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ቱሉ ጥላሁን (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ ከተማዋን ስማርት ሲቲ ለማድረግ የስምንት አመት ስትራቴጂክ ፕላን ተቀርጾ ወደ ስራ መገባቱን አንስተዋል።
ስትራቴጂ ፕላኑ መተግበር ከጀመረ ሁለት ዓመታትን ያስቆጠረ መሆኑን ጠቅሰው፣በዚህ ጊዜ ውስጥ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል።
ከእነዚህ ውስጥ የተቋማትን አሰራር በቴክኖሎጂ ማሳለጥ የሚያስችል የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግንባታ አንዱ ነው ብለዋል።
በአሁን ጊዜ ተቋማት በዲጂታል ቴክኖሎጂ እንዲገነቡና እንዲጠቀሙ በመደረጉ አገልግሎት አሰጣጡን ማቀላጠፍ የተቻለ መሆኑንም አመልክተዋል።
ለአብነትም በመሬት አስተዳደር፣ በሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት የመሳሰሉ ቁልፍ ተቋማትን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ለመደገፍ የተጀመረው አሰራር ውጤታማ መሆኑን አንስተዋል።
እንደ ምክትል ቢሮ ኃላፊው ገለጻ፣በከተማዋ የተከናወኑ የኮሪደር ልማቶች የስማርት ሲቲ ግንባታው ወሳኝ ሚና አላቸው።
የኮሪደር ልማቱን ጨምሮ በከተማዋ የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማዋ በአለም አቀፍ ደረጃ እውቅናና ተቀባይነት እንዲጨምር ማድረጉንም ነው የተናገሩት።
በአዲስ አበባ ሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዳይሬክተር አእምሮ ካሳ በበኩላቸው፣ ቀደም ሲል የነበረው የተቋሙ አሰራር ቴክኖሎጂ ባለመደራጀቱ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ተደጋጋሚ ቅሬታ ይነሳ እንደነበር አስታውሰዋል።
ተቋሙ ከ2016 ጀምሮ የዲጂታል ቴክኖሎጂ መገንባቱን ተከትሎ የሚሰጣቸውን አገልግሎት ከወረቀት ውጭ በማድረግ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል ነው ያሉት።
ከዚህም በተጨማሪ ቴክኖሎጂውን ከሌሎች ተቋማት ጋር በማስተሳሰር የአገልግሎት አሰጣጡን በማቀላጠፍ የነዋሪውን እንግልት በከፍተኛ ሁኔታ እየቀነሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
የአገልግሎት አሰጣጡን የበለጠ ለማቀላጠፍ ከሌሎች ተቋማት ጋር በቴክኖሎጂ የተሳሰረ ግንኙነት መፈጠሩንም አመልክተዋል።