ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ምርምር እና ስልጠና ላይ አተኩሮ እየሰራ ነው

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2017(ኢዜአ)፦ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በአቅም ግንባታ ስልጠና እና ምርምር ላይ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ አስታወቀ፡፡

ዩኒቨርሲቲው በክረምት መርኃ ግብር ብቻ ከ6 ሺ 500 ለሚልቁ መምህራን እና አመራሮች የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና መስጠቱ ተመላክቷል፡፡

ለትምህርት ጥራት መጓደል የትምህርት ዩኒቨርሲቲ አለመኖር እንደ ምክንያት ሲነሳ የቆየ ሲሆን ይህንኑ ችግር ለመቅረፍ ዩኒቨርሲቲው በአዋጅ ተቋቁሞ ወደ ስራ ገብቷል፡፡

የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ተልዕኮ ወስዶ ወደ ስራ ከገባ አንስቶ አመርቂ ውጤት አስመዝግቧል፡፡

በዚህም የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት ባለፉት ጥቂት አመታት ውጤታማ ተግባራትን ማከናወኑን አስታውቀዋል፡፡

የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የመምህራንን እና የአመራሮችን አቅም ማሳደግ ወሳኝ በመሆኑ የእቅም ግንባታ ላይ አተኩሮ እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ በትምህርት ሚኒስቴር ስር መምህራንን የሚያሰለጥኑ ባለሙያዎችን በስፋት እያስተማረ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲው ከክልል ትምህርት ቢሮዎች ጋር በመፈራረም የትምህርት ጥራትን የሚያረጋግጡ የምርምር ስራዎች እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

ለአብነትም ከአዲስ አበባ፣ ከኦሮሚያ እና ከአፋር ትምህርት ቢሮዎች ጋር በመፈራረም በርካታ የጥናትና የምርምር ስራዎች በመከናወን ላይ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲው የጀመረው ስራ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ባለድርሻ አካላት ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበዋል፡፡

የቀድሞው ኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ በ2014 ዓም ተጠሪነቱ ለትምህርት ሚኒስቴር ሆኖ በአዋጅ ወደ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ መቀየሩ ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም