የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ መንግስታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው - ግብርና ሚኒስቴር - ኢዜአ አማርኛ
የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ መንግስታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው - ግብርና ሚኒስቴር

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 1/2017(ኢዜአ)፡- መንግስት የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በዝርያ ማዳቀል፣ በመኖ ልማት፣ በወተት ማቀነባበርና በገበያ ትስስር ላይ መንግስታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ ግብርና ሚኒስቴር ገልጿል።
ባለፉት ዓመታት የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰሩ ስራዎች አበረታች ውጤት መመዝገቡን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ(ዶ/ር) ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የወተት ልማት ምርታማነት እና ኢኖቬሽን ላይ ያተኮረ ውይይት ዛሬ ተካሂዷል።
በዚሁ ወቅት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ(ዶ/ር) እንዳሉት የወተት ምርትን የበለጠ ማሳደግ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።
የወተት ምርታማነትን የበለጠ ለማሳደግ የባለድርሻ አካላት ትብብር ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
በቀጣይ ዘርፉን በምርምር መደገፍ፣ ስራዎችን በጋራ መስራት እና የሌሎች ሀገራት ተሞክሮዎችን በመቅሰም ተግባራዊ ለማድረግ እንደሚሰራም ጠቁመዋል።
የሌማት ትሩፋት መርኃ ግብር ከመጀመሩ በፊት ዓመታዊ የወተት ምርት 5 ነጥብ 8 ቢሊየን ሊትር እንደነበር ገልፀው በዚህ ዓመት መጨረሻ ዓመታዊ የወተት ምርትን 12 ቢሊየን ሊትር ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህ ዓመት 3 ነጥብ 8 ሚሊየን ላሞችን ለማዳቀል መታቀዱን አስታውቀው እስከ አሁን 2 ሚሊየን ላሞችን ማዳቀል መቻሉን ተናግረዋል።
መንግስት የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በዝርያ ማዳቀል፣ በመኖ ልማት፣ በወተት ማቀነባበር እና በገበያ ትስስር ላይ መንግስታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
የወተት ምርታማነትን በምርምር ለማሳደግ የወተት ላም ዝርያዎች ማሻሻል የሚያስችሉ ስራዎች በመስራት የተሻለ ውጤት መገኘቱን ጠቁመዋል።
ተጨማሪ አምስት አዳዲስ የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻ የዝርያ ማሻሻያ ማዕከላት በተለያዩ ከተሞች ስራ መጀመራቸውን ገልጸዋል።
በዚህም ላሞችን ከማዳቀል እስከ ወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች ግንባታ በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል።
የዓለም አቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት ከፍተኛ ተመራማሪ ዶክተር ገብረእግዚአብሔር ገብረዮሃንስ ከሚኒስቴሩ ጋር በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመደገፍ ዝርያ ለማሻሻል፣ የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።
ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የተጀመሩ ስራዎች የበለጠ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።