ኮሪደር ልማት የባሕር ዳር ከተማን እና የጣና ሐይቅን ውበት አጉልቷል - ኢዜአ አማርኛ
ኮሪደር ልማት የባሕር ዳር ከተማን እና የጣና ሐይቅን ውበት አጉልቷል
ባሕር ዳር፤ የካቲት 18/2017( ኢዜአ)፦ የኮሪደር ልማት የጣና ሐይቅን ውበት የገለጠ እና የባሕር ዳርን ቱሪስት መዳረሻነት የሚያጎላ ነው ሲሉ የገቢዎች ሚኒስትር አይናለም ንጉሴ ገለፁ።
ሚኒስትሯና ሌሎች የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች ኮሪደር ልማትን ጨምሮ የባሕር ዳር ከተማ የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።
ሚኒስትሯ እንዳሉት የኮሪደርና ሌሎች የልማት ስራዎች የጣናን ውበት የገለጡና ባሕር ዳርን የቱሪስት መዳረሻነት የሚያጎሉ ናቸው።
የኮሪደር ልማት የከተማዋ ነዋሪዎች የኑሮ ዘይቤ የሚያሻሽል እንደሆነም ገልፀዋል።
የባሕር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲዮም ግንባታ ዓለም አቀፍ ደረጃ በማሟላት ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ለማስተናገድ እየተገነባ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ለከተማዋ ተጨማሪ ፀጋ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ፤ በከተማዋ ሁለንተናዊ ጠቀሜታ ያላቸው የኮሪደር ልማትና ሌሎችም የልማት ፕሮጀክቶች እየተፋጠኑ መሆኑን መታዘባቸውን ገልጸዋል።
የልማት ፕሮጀክቶቹ የከተማዋን ውበት የሚገልጡ እና የዜጎችን ተጠቃሚነት እንደሚያሳድጉ ገልጸዋል።
በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ ክላስተር አስተባባሪና የአማራ ክልል ከተሞችና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር)፤ በክልሉ የከተሞችን ገፅታ የሚቀይሩ የኮሪደር የልማት ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል።
ባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደሴ፣ ኮምቦልቻና ደብረ ብርሃን ከተሞች ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ ኮሪደር እየተሸጋገሩ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ኮሪደር ልማት ከተሞችን ውብ፣ ተወዳዳሪና የቱሪስት መዳረሻ የሚያደርግና ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚ የሚያደርጉ ናቸውም ብለዋል።
የባሕር ዳር ኮሪደር ልማት በተያዘለት ጊዜ ገደብ አግባብ እየተከናወነ መሆኑን ደግሞ የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ተናግረዋል።
ስራው ከጣና ሐይቅ ጋር ተሳስሮ በጥራት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀው፤ የመጀመሪያው ምዕራፍ እየተጠናቀቀ መሆኑን አመልክተዋል።