በሰሜን ወሎ ዞን በጋዞ ወረዳ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተመረቁ - ኢዜአ አማርኛ
በሰሜን ወሎ ዞን በጋዞ ወረዳ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተመረቁ
ወልዲያ የካቲት 09/2017 (ኢዜአ) በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ጋዞ ወረዳ በመንግስትና በህዝብ ተሳትፎ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ።
ከተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች ውስጥም የአስተዳደር ምክር ቤት ህንፃን ጨምሮ ሶስት ጤና ጣቢያዎች፣ ስምንት የትምህርት ቤት ማሻሻያና የቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ ይገኝበታል።
በተጨማሪም ሰባት ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ፣ አነስተኛ የንፁህ መጠጥ ውሃ ተቋማት፣ የመስኖ ካናል ፣ ሁለት የእንስሳት ጤና ኬላና የእንስሳት ዝርያ ብዜት ማዕከላትና ሌሎችም ይገኙበታል።
የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በምረቃ ስነ-ስርዓ ላይ እንደገለጹት የተገነቡት የልማት ፕሮጀክቶች የህብረተሰቡን ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ናቸው።
ፕሮጀክቶቹን ጠብቆ ለረጅም ጊዜ ለመጠቀምና አዳዲስ ፕሮጀክቶችን ለማስጀመር የልማት መሠረት የሆነውን ሠላም ማጽናት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የክልሉ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬ በበኩላቸው የተመረቁትና በጉብኝት የታዩት የልማት ፕሮጀክቶች በአመራሩና በህዝቡ ቁርጠኝነት የተከናወኑ ናቸው ብለዋል።
አሁንም ሠላምን ይበልጥ በማጽናት የህዝብን ተጠቃሚነት በምናረጋግጥበት ልማት ላይ ይበልጥ መስራት ይገባል ሲሉም አክለዋል።
የሰሜን ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አራጌ ይመር በበኩላቸው በዞኑ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ በርካታ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በቀጣይም አሁን የሚታየውን የተሻለ ሠላም ይበልጥ በዘላቂነት በማረጋገጥ የዞናችንን ልማት ለማፋጠን በቁርጠኝነት ከህብረተሰቡ ጋር በጋራ እንሰራለን ብለዋል።
በምረቃ ስነ- ስርዓቱ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ የአመራር አባላት እንዲሁም ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።