ተሰናባቹ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋቂ ማህማት ፦

 

✅ ቻዳዊው ዲፕሎማትና ፖለቲከኛ ሙሳ ፋቂ ማህማት እ.አ.አ ሰኔ 21 ቀን 1960 በምስራቃዊ ቻድ በምትገኘው ቢልታይን ከተማ ተወለዱ፤

✅እ.አ.አ በ1986 በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በኮንጎ ሪፐብሊክ ብራዛቪል በሚገኘው ማሪየን ኑጉዋቢ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል፤

✅ከእ.አ.አ ከ1996 እስከ 1999 የቻድ ብሔራዊ የስኳር ኩባንያ (ሶናሱት) ዋና ዳይሬክተር በመሆን አገልግለዋል፤

✅እ.አ.አ ከ1999 እስከ 2002 የቻድ ፕሬዚዳት የካቢኔ ጉዳዮች ዳይሬክተር በመሆን ያገለገሉ ሲሆን፣ እ.አ.አ በ2001 በቻድ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የእድሪስ ዴቢ የምርጫ ቅስቀሳ ሃላፊ ነበሩ፤

✅እ.አ.አ በወቅቱ የቻድ ጠቅላይ ሚኒስትር በነበሩት ሃሩን ካባዲ ተመርጠው በ2001 የቻድ የትራንስፖርት ሚኒስትር በመሆን ለአንድ ዓመት ሰርተዋል፤

✅የቀድሞው የቻድ ፕሬዚዳንት ኢድሪስ ዴቤ ሙሳ ፋቂ ማህማትን በሃሩን ካባዲ ቦታ በመተካት እ.አ.አ በ2003 የአገሪቷ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገው ሾመዋቸዋል፤

✅እ.አ.አ በ2008 በወቅቱ የቻድ ጠቅላይ ሚኒስትር የሱፍ ሳሌህ አባስ የሚመራው መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሆናቸውን ይፋ ያደረገ ሲሆን፤ እ.አ.አ እስከ 2017 የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ሰርተዋል፤

✅ሙሳ ፋቂ ማህማት እ.አ.አ በ2017 በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበርነት ምርጫ በመወዳደር ተፎካካሪያቸው የነበሩትን ኬንያዊቷን ዲፕሎማት አሚና ሞሐመድን በማሸነፍ የሕብረቱ ሊቀመንበር ሆነው ተመረጡ፤

✅የቻዱ ዲፕሎማት የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሆነው ሲመረጡ በአፍሪካ ሰላምና ልማት ላይ ትኩረታቸውን አድርገው እንደሚሰሩ ገልጸው ነበር።

✅ሙሳ ፋቂ ማህማት እ.አ.አ በ2021 ለአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበርነት በተደረገው ምርጫ ብቻቸውን ለእጩነት ቀርበው በድጋሚ የኮሚሽኑ ሊቀመንበር ሆነው በመመረጥ ለአራት ዓመት አገልግለዋል።

✅ከፓሪስ ዩኒቨርሲቲ በሕግ የዶክትሬት ዲግሪ ያገኙት የ61 ዓመቱ ዲፕሎማት ሙሳ ፋቂ ማህማት የቻድ ገዢ ፓርቲ ‘ፓትሪዮቲክ ሳልቬሽን ሙቭመንት’ አባል ሲሆኑ፤ ከ30 ዓመት በላይ በዲፕሎማሲና ፖለቲካ ዘርፍ አገልግሎት አላቸው።

✅ሙሳ ፋቂ የስምንት ዓመት የስራ ዘመናቸውን ዛሬ አጠናቀዋል።

✅ዛሬ በአዲስ አበባ መካሄድ በጀመረው የ38ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ የጅቡቲው የውጭ ጉዳይ እና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር መሐሙድ አሊ የሱፍ ዛሬ የህብረቱ ኮሚሽን ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠዋል።

✅ሚኒስትሩ የቻዱን ዲፕሎማት ቦታ በይፋ ተረክበው ለቀጣይ አራት ዓመታት ያገለግላሉ።

✅ሙሳ ፋቂ ማህማት የአምስት ልጆች አባት ሲሆኑ፤ ፈረንሳይኛ፣ አረብኛና እንግሊዘኛ ቋንቋን አቀላጥፈው ይናገራሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም