ቀጥታ፡

የሀገርና የሕዝብ ኩራትና አለኝታ የሆነ አየር ኃይል ተገንብቷል - ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ

አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2017 (ኢዜአ):- አየር ኃይል የሀገር ኩራት፣ የህዝብ አለኝታ መሆን እንዲችል ተደርጎ ተገንብቷል ሲሉ የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ ገለጹ።

ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ በመከላከያ አዛዥነት እና ስታፍ ኮሌጅ ከ15ኛ ዙር መደበኛ ተማሪ ከፍተኛ መኮንኖች ጋር ተወያይተዋል፡፡


 

ዋና አዛዡ ለከፍተኛ መኮንኖቹ ባደረጉት ገለፃ ተቋሙ የአመራሮችን አቅም የሚያጎለብቱ በርካታ ተግባራት እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።

በዚህም ብቃትና ጥራት ያላቸውን ተተኪ ወታደራዊ አመራሮች እያፈራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

አየር ኃይል የሃገር ኩራት፣ የህዝብ አለኝታ መሆን እንዲችል ተደርጎ መገንባቱን ተናግረዋል።

ከአፍሪካ አየር ኃይሎች ቀዳሚው ለማድረግ በከፍተኛ ንቅናቄ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚስ ግብ ስኬት የአመራሮች ሚና ጉልህ መሆኑን አንስተዋል።

የመከላከያ አዛዥነት እና ስታፍ ኮሌጅ አዛዥ ብርጋዲየር ጄኔራል ሙሉጌታ አምባቸው በበኩላቸው ኮሌጁ የመከላከያን የተማረ የሰው ኃይል ፍላጎት መሰረት በማድረግ በርካታ አመራሮችን በማስተማር የሠራዊቱን ግዳጅ የመፈፀም አቅም እያጠናከረ ይገኛል ብለዋል፡፡

ከፍተኛ መኮንኖቹ የአየር ኃይሉን የለውጥ ጉዞና አሁናዊ ወታደራዊ ቁመናውን እንዲሁም የቴክኖሎጂ አቅሙን ተዘዋውረው መመልከታቸውን ከአገር መከላከያ ሰራዊት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም