ቀጥታ፡

የድል ዓርማ የሆነው ሕዳሴ ግድብ እስኪጠናቀቅ በአንድነት መጽናት ይገባል- ዑስታዝ ጀማል በሽር

አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያውያን የድል ዓርማ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እስኪጠናቀቅ በአንድነት መጽናት ይገባናል ሲሉ የሕዳሴ ግድብ ተሟጋች ዑስታዝ ጀማል በሽር ጥሪ አቀረቡ።

ኢትዮጵያ በድንበር ተሻጋሪ ወንዞች የጋራ ተጠቃሚነት መርህ ለቀጣናዊ ትስስር አበክራ እየሰራች እንደሆነ ዑስታዝ ጀማል ገልጸዋል።

በታላቁ ሕዳሴ ግድብ እና በዓባይ ወንዝ ፖለቲካ ላይ በመሟገት የሚታወቁት እና ትኩረቱን በዚሁ ጉዳይ ባደረገው የዓባይ ንጉሦች የተሰኘው ሚዲያ ባለቤት ዑስታዝ ጀማል በሽር ግድቡ ብሔራዊ ኩራትና የድል ዓርማችን ነው ብለዋል።

ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገራት ለጋሽ እንጂ አንድ ጠብታ ውሃ ተቀባይ ሀገር ባትሆንም በጋራ ልማት ግን ቀዳሚ ተሰላፊ ሀገር ናት ይላሉ።

ለአብነትም በዑጋንዳው ኢንተቤ የተደረሰው የናይል ወንዝ ተፋሰስ ሀገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ስራ ላይ እንዲውል የመሪነት ሚና በመወጣት የነበራትን አበርክቶ ጠቅሰዋል።

የትብብር ማዕቀፍ ስምምነቱ ለተፋሰሱ ሀገራት ፍትሕዊ የውሃ ሃብት አጠቃቀም ስርዓትን ለመዘርጋት ጉልህ ፋይዳ እንዳለውም እንዲሁ።

በታዳሽ ኃይል ልማትና አቅርቦቷም የአፍሪካ የመሰረተ ልማት ትስስርን ዕውን ለማድረግ ያላትን ቁርጠኝነት ሁነኛ ያሳየ ነውም ብለዋል።

ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያዊያን ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ጫና ሳንበገር ዕውን ያደረግነው ብሔራዊ የድል ዓርማ ብለውታል።

ፕሮጀክቱ በመላ ኢትዮጵዊያን አሻራ የተገነባ፣ ኢኮኖሚያዊ አበርክቶው የጎላ እና ብሔራዊ ጥቅም ማረጋገጫ ፕሮጀክት ነው ብለዋል።

አሁንም ቢሆን ግድብ እስኪጠናቀቅ መላው ኢትዮጵያዊያን በገንዘብና በዲፕሎማሲ ድጋፍ በአንድነት ጸንተው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል።

ውስጣዊ ችግሮችን በምክክር ሂደት መፍታት እንደሚገባ ገልጸው፤ በብሔራዊ ጥቅም ላይ ግን በጋራ መቆምና መተባበር እንደሚሻ ተናግረዋል።

በመሆኑም ብሔራዊ የድል ዓርማ በሆነው ሕዳሴ ግድብ የተለዬ አቋም ሊኖር እንደማይገባ ነው ያነሱት።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም