የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የ3ኛ ዙር የሳይበር ታለንት ሰመር ካምፕ ሰልጣኞችን አስመረቀ - ኢዜአ አማርኛ
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የ3ኛ ዙር የሳይበር ታለንት ሰመር ካምፕ ሰልጣኞችን አስመረቀ
አዲስ አበባ፤ ጥር 3/2017(ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በ3ኛው ዙር የሳይበር ታለንት ሰመር ካምፕ ፕሮግራም ያሰለጠናቸውን ሰልጣኞች አስመረቀ።
አስተዳደሩ የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ የቅዳሜና እሁድ የስልጠና ፕሮግራም ከተለያዩ ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ ተማሪዎች መስጠት ጀምሯል።
የሳይበር ታለንት ሰመር ካምፕ ስልጠናቸውን አጠናቀው ለምረቃ የበቁት ከመላ ኢትዮጵያ የተውጣጡ 237 ባለልዩ ተሰጥኦ ወጣቶች ናቸው።
የአስተዳደሩ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳንኤል ጉታ በዚሁ ጊዜ፥ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ብቃት ያለው የሳይበር ባለሙያ በብዛትና በጥራት ማፍራት ያስፈልጋል ብለዋል።
አስተዳደሩ ከመላ ኢትዮጵያ የተውጣጡ ባለልዩ ተሰጥኦ ታዳጊዎችን በሳይበርና ተያያዥ ጉዳዮች እያበቃ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
ተለዋዋጭ የቴክኖሎጂ ዕድገትን የሚመጥንና የሳይበር ጥቃትን ለመከላከል ብቁና ተወዳዳሪ ባለሙያ የማፍራት ጥረቱ ይቀጥላል ብለዋል።
በአስተዳደሩ የሳይበር ማዕከል ዳይሬክተር ቢሻው በየነ በበኩላቸው ከሀገራዊ ለውጡ በኃላ ለባለተሰጥኦ ወጣቶች ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህም ማዕከሉ ከሳይበር ደህንነት ጋር በተያያዘ የሚሰጠው ስልጠና ተደራሽነት እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል።
ሰልጣኞቹ በበኩላቸው በስልጠናው መሰረታዊ የዲጂታል ዕውቀት ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል።