የአርባምንጭ ከተማ የኮሪደር ልማት የነዋሪዎችን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች በሚመልስና የቱሪስት ፍሰትን በሚያሳድግ መልኩ እየተከናወነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የአርባምንጭ ከተማ የኮሪደር ልማት የነዋሪዎችን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች በሚመልስና የቱሪስት ፍሰትን በሚያሳድግ መልኩ እየተከናወነ ነው
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2017(ኢዜአ)፦ የአርባምንጭ ከተማ የኮሪደር ልማት የነዋሪዎችን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች በሚመልስና የቱሪስት ፍሰትን በሚያሳድግ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን የከተማዋ አስተዳደር ከንቲባ ገዛኸኝ ጋሞ ገለፁ።
የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባሻገር ለነዋሪዎች ምቹ አካባቢን ለመፍጠር የሚያስችል መሆኑንም ገልፀዋል።
አገራት በከተሞች ከሕዝብ ቁጥር መጨመር ጋር ተያይዞ የሚስተዋለውን የሰዎች የተለያዩ አገልግሎቶችን የማግኘት ከፍተኛ ፍላጎት ለማሟላት እና የዜጎችን ኑሮ ቀላል ለማድረግ ከተሞቻቸውን ዘመናዊ አድርገው በመገንባት ትልቁን ሚና እየተጫወቱ ይገኛል።
በኢትዮጵያም ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ አዲስ አበባን ጨምሮ ሌሎች የክልል ከተሞችን ዘመናዊና ለዜጎች ምቹ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል።
በመጀመሪያ ዙር በአዲስ አበባ የተከናወነው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ እንዲቀየርና ተወዳዳሪነቷ እንዲያድግ ተጨማሪ አቅም ፈጥሯል።
ይህም መልካም ተሞክሮ በሌሎች የክልል ከተሞች በማስፋት በልዩ ትኩረት እየተሰራ ይገኛል።
የአርባምንጭ ከተማም የኮሪደር ልማት እየተከናወነባቸው ከሚገኙ ከተሞች አንዷ ስትሆን የከተማዋን ነዋሪዎች የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች በሚመልስና የቱሪስት ፍሰትን በሚያሳድግ መልኩ እየተገነባ መሆኑን የከተማው ከንቲባ አቶ ገዛኸኝ ጋሞ ለኢዜአ ተናግረዋል።
የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባሻገር ለነዋሪዎች ምቹ አካባቢን ለመፍጠር የሚያስችል እንደሆነም ገልጸዋል።
በዚህም በመጀመሪያ ዙር 9 ነጥብ 6 ኪሎ ሜትር የመንገድ ኮሪደር መልማቱን ተናግረዋል።
ይህም ምቹ የእግረኛ መንገድ፣ አረንጓዴ ቦታዎችን ያካተተ እና የመንገድ መብራት መሰረተ ልማት የተዘረጋላቸው እንደሆኑ ጠቅሰዋል።
በሁለተኛው ምዕራፍ ከአዲስ አበባ ልምድ በመቅሰም በመጀመሪያ ምዕራፍ ያልተካተቱ የሳይክል መንገድን ጨምሮ የተለያዩ መሠረተ ልማት ያለው ኮሪደር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
ኮሪደሩ አርባምንጭ ያላትን የተፈጥሮ ውበት የበለጠ ማሳመርና መንከባከብን ትኩረት ያደረገ መሆኑን ከንቲባው ገልፀዋል።
ከተማዋ ፈጣን ዕድገት ላይ እንዳለች የተናገሩት ከንቲባው በከተማዋ የሚሰሩ የልማት ሥራዎች ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ነው ብለዋል።