ቀጥታ ስርጭት

የዩናይትድ ኪንግደም ሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ እና የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት በደኅንነትና ጸጥታ ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ የሚያከናውናቸውን የትብብር ሥራዎች ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ ተስማሙ

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 13/2017(ኢዜአ)፦ የዩናይትድ ኪንግደም ሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ እና የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት በደኅንነትና ጸጥታ ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ የሚያከናውናቸውን የትብብር ሥራዎች ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ ተስማሙ

በዩናይትድ ኪንግደም ሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ (MI6) ሀላፊ ሰር ሪቻርድ ፒተር ሙር የተመራ የልዑካን ቡድን ለሥራ ጉብኝት አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ በሀላፊው በሰር ሪቻርድ ፒተር ሙር የተመራው ልዑክ በቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከፍተኛ አመራሮች አቀባበል አድርገውለታል።


 

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ አመራሮችና የሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ (MI6) ልዑካን በተቋማት ደረጃ በሚከናወኑ የሁለትዮሽ ጉዳዮች እንዲሁም በቀጣናዊ፣ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ዙሪያ በስፋት ተወያይተዋል።

በውይይቱ ወቅትም ቀጣናዊ፡አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች በተለይም ደግሞ የቀይ ባሕር ወቅታዊ ጉዳይ፣ የደኅንነትና የጸጥታ ስጋት የሆኑቱን ሽብርተኝነት፣ ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎችንና ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውርን በቅንጅት ለመከላከል በቀጣይ የሚደረጉ የመረጃ ልውውጥ ስራዎች መዳሰሳቸውን የአገልግሎት መስሪያ ቤቱ መረጃ ያመለክታል፡፡

በውይይቱ ላይ የተገኙት የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሲሳይ ቶላ ኢትዮጵያ የባህር በር ተደራሸርነት እንዲኖራት የጀመረቸውን እንቅስቃሴ አንዳንድ አካላት ሆን ብለው ለሀሰት ፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ለመጠቀም እየሞከሩ መሆኑና ይህ ደግሞ ቀጠናው እንዳይረጋጋ እና ዘላቂ ሰላም እንዳይሰፍን አሉታዊ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ለሀላፊው አብራርተውላቸዋል፡፡

አቶ ሲሳይ የሁለቱ ተቋማት ግንኙነት በቀጠናው እያደገ ካለው አዲስ ሁኔታ ጋር እንዲጣጣም በጋር መስራት እንዳልባቸውም ገልፅዋል፡፡ በቀጠናው ያለው ያልተረጋጋ ሁኔታ ወደ ተረጋጋ ሰላማዊ ሁኔታ እንዲቀየር ኢትዮጵያ ወሳኝ ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ እና እንደምትወጣም ጭምር ለዩናይትድ ኪንግደም ሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ (MI6) ሀላፊ ማረጋገጣቸውን የብሄራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት መረጃ ይጠቁማል፡፡

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሲሳይ ቶላ አክለውም የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ፤ የቀጠናው አገራት በትብብር እንዲሰሩ የሚያበረታታ እንጂ የልዩነት፡ የንትርክና የግጭት አጀንዳ መሆን እንደሌለበት አፅኖኦት ሰጥተው መናገራቸውን የአገልግሎት መስሪያ ቤቱ መረጃ ያመለከታል፡፡

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከቀጣናው ሀገራት እንዲሁም ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራትና ዓለምአቀፍ አቻ የመረጃ ተቋማት ጋር ጠንካራ የመረጃ ልውውጥ፣ የአጋርነትና የትብብር ሥራዎቹን እየሰራ መሆኑን የገለፁት አቶ ሲሳይ ቶላ፤ ከዩናይትድ ኪንግደም ሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ ጋር ያለውን ትብብርም ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገርና ማጠናከር እንደሚፈልግ መግለፃቸውን መረጃው ይጠቁማል፡፡

የኤም አይ ሲክስ ሴክሬት ኢንተለጀንስ ሰርቪስ ሀላፊ ሰር ሪቻርድ ፒተር ሙር በበኩላቸው ኢትዮጵያ ካላት ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እና ተጽዕኖ ፈጣሪነት አንፃር በቀጣናዊ፣ አህጉራዊና እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ዙሪያ ተቋማቸው በደኅንነትና ጸጥታ ጉዳዮች ዙሪያ እያደረገ ያለውን የመረጃ ልውውጥ እንዲሁም በቴክኖሎጂ እና በአቅም ግንባታ መስኮች የጀመራቸውን የትብብር እና አጋርነት ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ማረጋገጣቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መረጃ አመልክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም