የተተከሉ ችግኞችን መንከባከብና መከታተል ይገባል- ብሔራዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዓቢይ ኮሚቴ - ኢዜአ አማርኛ
የተተከሉ ችግኞችን መንከባከብና መከታተል ይገባል- ብሔራዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዓቢይ ኮሚቴ

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2017(ኢዜአ)፦ የተተከሉ ችግኞችን መንከባከብና መከታተል እንደሚገባ ብሔራዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዓቢይ ኮሚቴ አሳሰበ።
ዓቢይ ኮሚቴው የ2016 በጀት ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አፈፃፀምና የ2017 በጀት ዓመት መነሻ ዕቅድን ገምግሟል።
የ2016 በጀት ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አፈፃፀም ጥሩ ውጤት የታየበት መሆኑን የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
በ2017 በጀት ዓመት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የችግኝ ተከላ ወቅት ጥራት ላይ ትኩረት በማድረግ መስራት እንደሚገባም አመልክተዋል።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር ኢ/ር) በበኩላቸው አረንጓዴ አሻራን በሳይንሳዊ መንገድ በመደገፍ ያመጣውን ለውጥ ማጠናከር፣ የመረጃ አያያዝ ስርዓትን ማዘመንና የክልሎችን አቅም ማሳደግ ላይ በቅንጅት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል።
በ2017 በጀት ዓመት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የችግኝ ተከላ ከ2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በላይ የተከላ ቦታ ልየታና የካርታ ዝግጅት ለመስራት በዕቅድ መያዙም ተገልጿል።
በ2016 በጀት ዓመት 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ታቅዶ “የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ” በሚል መሪ ቃል ከ7 ነጥብ 5 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከል መቻሉ ተጠቁሟል።
ባለፉት ስድስት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከ40 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከል መቻሉንና እስከ 2018 ዓ.ም ባለው ጊዜ የሚተከለውን ችግኝ ወደ 50 ቢሊዮን ለማድረስ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ከግብርና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።