ባለፉት አሥር ወራት በዋና ዋና የማክሮ ኢኮኖሚ ዘርፎች የተመዘገበው ስኬት የ7 ነጥብ 9 በመቶ እድገት እንደሚመዘገብ አመላካች ነው - ኢዜአ አማርኛ
ባለፉት አሥር ወራት በዋና ዋና የማክሮ ኢኮኖሚ ዘርፎች የተመዘገበው ስኬት የ7 ነጥብ 9 በመቶ እድገት እንደሚመዘገብ አመላካች ነው
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2016(ኢዜአ)፦ ባለፉት አሥር ወራት በዋና ዋና የማክሮ ኢኮኖሚ ዘርፎች የተመዘገበው ስኬት የ7 ነጥብ 9 በመቶ እድገት እንደሚመዘገብ አመላካች መሆኑ ተገለጸ።
የበጀት ዓመቱ የመጨረሻው የ100 ቀናት አፈጻጸም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት እየተካሄደ ነው።
የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ(ዶ/ር) በመድረኩ ያለፉት 100 ቀናት እና የሁለተኛው ሀገር በቀል ኢኮኖሚ አፈጻጸም እንዲሁም የ2017 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ሪፖርት አቅርበዋል።
በዚህም ባለፉት አሥር ወራት የ3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን ተናግረዋል።
ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ14 ነጥብ 3 በመቶ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል።
በተጨማሪም መንግሥት 425 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን ገልጸው፤ ከዚህም ውስጥ 271 ቢሊዮን ብሩ ከሀገር ውስጥ ገቢ የተሰበሰበ ነው።
ከሸቀጦች የወጪ ንግድ 2 ነጥብ 9 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱንም እንዲሁ።
በተጨማሪም ከሬሚታንስ 4 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን የተናገሩት ሚኒስትሯ፤ የመንግሥት የበጀት ጉድለትም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ14 በመቶ መቀነስ መቻሉን ገልፀዋል።
በተጠቀሰው ወራት ለ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች በሀገር ውስጥ እንዲሁም ከ300 ሺህ በላይ ለሚሆኑት ደግሞ በውጭ ሀገራት የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል።
በአጠቃላይ በዋና ዋና የማክሮ ኢኮኖሚ አመላካቾች የተመዘገበው ስኬት ኢትዮጵያ የ7 ነጥብ 9 በመቶ እድገት እንደምታስመዘግብ አመላካች መሆኑን አብራርተዋል።