ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የሚያግዛትን 5ኛ ዙር ድርድር በግንቦት ወር ታካሂዳለች- አቶ ገብረ መስቀል ጫላ 

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 29/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የሚያግዛትን 5ኛ ዙር ድርድር በግንቦት ወር ልታካሂድ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ገብረ መስቀል ጫላ ገለፁ።

አቶ ገብረ-መስቀል ጫላ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ከ20 ዓመታት በፊት የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን እንቅስቃሴ ጀምራለች።

ይሁንና በኮቪድ-19 ወረርሽኝና በሌሎች ምክንያቶች ድርድሩ ተቋርጦ እንደነበር የሚታወስ ነው። 

ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የጀመረችውን ጥረት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ከቆመበት ለማስቀጠል የተለያዩ ተግባራት እያከናወነች መሆኗን አስታውቀዋል።

ይህንንም ተከትሎ የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን በሐምሌ 2015 ዓ.ም ወደ ጄኔቫ አቅንተው ከድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸውን አስታውሰዋል።

በውይይቱም ኢትዮጵያ በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ የድርድር ሂደቱ እንዲጠናቀቅና የድርጅቱ አባል እንድትሆን ከሥምምነት መደረሱን ነው ያስታወሱት።  

በዚህም ከኢትዮጵያ ጋር ድርድር ለማድረግ ፍላጎት ካላቸው ከአባል አገራቱ 180 የሚጠጉ ጥያቄዎችና 9 ሰነዶች መቅረባቸውን ተናግረዋል።

በቅርብ ጊዜ ውስጥ ድርጅቱ በሚያመቻቸው መድረክ ድርድሩ እንደሚጀመር ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል እንድትሆን የአገሪቱን ጥቅም በሚያስጠብቅ እንዲሁም የኢኮኖሚ ልማትና የንግድ ተወዳዳሪነት በሚያረጋግጥ አግባብ ለመደራደር ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ አስረድተዋል።

ኢትዮጵያ በዓለም ንግድ ድርጅት ውስጥ በታዛቢነት መሳተፍ የጀመረችው እንደ አውሮፓውያኑ አቆጠጣር በ2003 ነበር። 

ኢትዮጵያ የድርጅቱ አባል ለመሆን የእቃዎችና የአገልግሎት ንግድ ኦፈር፣ የገቢ ንግድ ፈቃድ አሰራር መረጃዎች ፣ የመንግሥት የንግድ ድርጅቶች መረጃ፣ ንግድና ንግድ ነክ ሕጎች መርኃ ግብር እንዲሁም የወጪ ንግድ ድጎማና የግብርና ምርቶች ድጋፍ ሰነዶችን የማሟላት ሥራ እየሰራች መሆኗን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። 

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም