የአሜሪካ የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደር በቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ያደረገውን የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ኦዲት በስኬት አጠናቀቀ-የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2016(ኢዜአ)፦ የአሜሪካ የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደር በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ያደረገው የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ኦዲት በስኬት መጠናቀቁን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ።

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፤ የአሜሪካ የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደር (TSA) ከመጋቢት 23 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ለአምስት ተከታታይ ቀናት በቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ኦዲት ሲያከናውን ቆይቷል፡፡

የኦዲት ልዑክ ቡድኑ በቆይታው የመንገደኞች፣ የሻንጣ፣ የካርጎ ጭነቶች፣ የዙሪያ ጥበቃና ፍተሻ እንዲሁም የአውሮፕላን ደኅንነትን ለማረጋገጥ የሚወሰደው የሴኪዩሪቲ እርምጃ ከዓለም አቀፍ አሰራር አንጻር አጠቃላይ ያለበትን ደረጃ በተመለከተ ሁሉን አቀፍ ኦዲት አድርጓል፡፡


 

በኦዲቱ ጥልቅ የሠነድ ግምገማ እና የአካል ምልከታ የተደረገ ሲሆን፤ በልዑኩ በቀረበው የማጠቃለያ ሪፖርት ወደ አሜሪካ ሀገር በሚደረጉ በረራዎችም ሆነ አጠቃላይ በአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ኦፕሬሽናል ሂደቶች ላይ ምንም ዓይነት የደኅንነት ስጋት እንደሌለ በድጋሚ መረጋገጡ ተገልጿል፡፡

በኢትዮጵያ ጠንካራ የሆነ የኢቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ስርዓት መገንባቱን እንዲሁም በቀጣይም በአፍሪካ ምርጥ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አገልግሎት ሰጪ ተቋም ለመሆን የተያዘውን ስትራቴጂክ ዕቅድ ለማሳካት የሚያስችል መሰረት እንደተጣለ የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደር (TSA) ተወካይ ገልጸው በሁለቱ ተቋማት ብሎም ሀገራት መካከል በዘርፉ የሚደረገው ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡

በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የሲቪል አቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ ዳይሬክተር አቶ አስራት ቀጀላ የኦዲት ሪፖርቱ በቀረበበት መርሐ ግብር ባደረጉት ንግግር በአገልግሎት መስሪያ ቤቱ በተሰጠው ልዩ ትኩረት በሲቪል አቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ የተደረገው ሁሉን አቀፍ ሪፎርም፣ የተዘረጋው አሰራር፣ የሰው ኃይል ልማት፣ የቴክኖሎጂ እምርታ እና ከምንጊዜውም በላይ የተጠናከረው የኤርፖርት ባለድርሻ አካላት ቅንጅት የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደርን (TSA) እና ከዚህ ቀደም የተደረጉ ሌሎች ተከታታይ ዓለም አቀፍ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ምዘናዎችን ስኬት ለመጎናፀፍ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አንደነበራቸው ገልፀዋል፡፡

በኦዲቱም ለተገኘው ሀገራዊ ውጤት ሌት ተቀን ሲተጉ ለነበሩ የዋና መምሪያው ሠራተኞችና አመራሮች እንዲሁም በኤርፖርት ለሚገኙ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

በቀጣይም በሚደረገው ሀገራዊ የዓለም አቀፍ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት (ICAO) ኦዲት ሁሉም በከፍተኛ ቅንጅት፣ ቁርጠኝነት እና ትብብር በመስራት ኢትዮጵያን በከፍታ ማስጠራት እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ለሀገራዊ ኦዲቱም ከወዲሁ ስራዎች ተለይተው እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡


 

የአሜሪካ የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደር ከሐምሌ 10 እስከ ሐምሌ 12 ቀን 2015 ዓም ድረስ ለተከታታይ ሦስት ቀናት በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ባካሄደው የበረራ ደኅንነት ልዩ ኦዲት በዓለም አቀፍ አሰራር መሰረት ምንም አይነት የደኅንነት ክፍተት (ግኝት) እንደሌለበት መግለጹ ይታወሳል፡፡

የአሜሪካ የትራንስፖርት ደኅንነት አስተዳደር ሐላፊ ዴቪድ ፕኮስኬ የኦዲት ውጤት መገኘቱን ተከትሎ ነሐሴ 28 ቀን 2015 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በተቋሙ ባደረጉት ጉብኝት ለኢትዮጵያ የበረራ ደኅንነት አጠባበቅ አድናቆታቸውን መግለጻቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለመገናኛ ብዙኃን የላከው መረጃ አመልክቷል፡፡

በመጨረሻም በዋና መምሪያው የተጀመረውን ሪፎርም አጠናክሮ በማስቀጠልና በኤርፖርቱ የሚገኙ ሁሉንም በለድርሻ አካላት አቀናጅቶ በማነቃነቅ ለህብረተሰቡ ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት አሰራሮች ተዘርግተው እየተተገበሩ መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጠቁሟል።

ተገልጋዩ በኤርፖርቱ ማህበረሰብ ከሚሰጡ አገልግሎቶቾ ጋር በተያያዘ አስተያየትና ቅሬታ ሲኖረው በኤርፖርት ውስጥ በተዘረጋው የአስተያየትና የጥቆማ መስጫ ስርዓት በግልጽ ሀሳቡን በመስጠት የተሻለ አገልግሎቶች ማግኘት እንዲችል በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም