ኢትዮጵያ የዓለም የሥራ ድርጅት አባል የሆነችበትን 100ኛ ዓመት በማስመልከት ሀገር አቀፍ ጉባኤ ሊካሄድ ነው

አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓለም የሥራ ድርጅት (ILO) አባል የሆነችበትን 100ኛ ዓመት በማስመልከት ሀገር አቀፍ ጉባዔ ሊካሄድ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ።  

የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ሙፈሪሃት ካሚል የጉባኤውን መካሄድ በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል።

ጉባኤው "ማህበራዊ ምክክርን እና የጎለበተ ምርታማነትን በመጠቀም ማህበራዊ ፍትህን ማላቅ" በሚል መሪ ሃሳብ ከኅዳር 24 እስከ 26 ቀን 2016 ዓ.ም በተለያዩ ኩነቶች ይካሄዳል ብለዋል።  

በጉባዔው ባለድርሻ አካላት በጋራ ሆነው ስኬቶች የሚገመገሙበት፣ ልምዶች የሚቀመሩበት ለዘርፉ መጠናከር የሚያግዙ ምክረ ሀሳቦች የሚንሸራሸሩበት ይሆናል ብለዋል።       

የዓለም ሥራ ድርጅት ሲቋቋም ኢትዮጵያ ከአፍሪካ በቀዳሚነት አባል መሆኗን አስታውሰው ይህም ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የትብብር መድረኮች ላይ ሁሌም ግንባር ቀደም ሚና እንደምትጫወት ማሳያ ነው ሲሉም ተናግረዋል።    

በመስኩ ሥራቸውን በአግባቡ በመከወን ውጤታማ መሆን የቻሉ አካላትና ሠራተኞች ዕውቅና የሚሰጥበት መርሃ ግብር መዘጋጀቱንም አስታውቀዋል።      

በጉባዔው ከዓለም የሥራ ድርጅት ጋር ያለውን ትብብር እና ስኬቶች፣ የገጠሙ ተግዳሮቶች የሚፈታበት አቅጣጫ ላይ የጋራ ሀሳብ የሚያዝበት መሆኑንም ገልጸዋል።      

 

 

 

 

  

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም