በላቲቪያ ሪጋ በሚካሄደው የዓለም የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በ13 አትሌቶች ተወከላለች - ኢዜአ አማርኛ
በላቲቪያ ሪጋ በሚካሄደው የዓለም የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በ13 አትሌቶች ተወከላለች

አዲስ አበባ፤ መስከረም 19/2016(ኢዜአ)፡- በላቲቪያ ሪጋ ለመጀመሪያ ጊዜ ዛሬ በሚደረገው የዓለም ጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና ኢትዮጵያን ወክለው 13 አትሌቶች ይሳተፋሉ።
በሻምፒዮናው ከ57 አገራት የተወጣጡ 347 አትሌቶች የሚሳተፉ ሲሆን 1 ማይል፣ 5 ኪሎ ሜትር እና የግማሽ ማራቶን በሁለቱም ጾታዎች ውድድር የሚካሄድባቸው ርቀቶች ናቸው።
ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በ7 ሴቶች እና በ6 ወንዶች በድምሩ በ13 አትሌቶች ትወከላለች።
በሴቶች 5 ኪሎ ሜትር እጅጋየሁ ታዬ እና መዲና ኢሳ ከቀኑ 5 ሰዓት ከ50 ላይ ውድድራቸውን ያደርጋሉ።
ከቀኑ 6 ሰዓት ከ15 ላይ በሚካሄደው ወንዶች ውድድር ዮሚፍ ቀጄልቻ እና ሐጐስ ገብረ ሕይወት ይወዳደራሉ።
ድርቤ ወልተጂና ፍሬወይኒ ኃይሉ 7 ሰዓት ላይ በሚካሄደው የአንድ ማይል እንዲሁም በወንዶች በተመሳሳይ ርቀት ከቀኑ 7 ሰዓት ከ10 ሰዓት ላይ በሚደረገው ውድድር ታደሰ ለሚ ይወዳደራል።
በሴቶች የግማሽ ማራቶን ውድድር ከቀኑ 7 ሰዓት 30 ጽጌ ገብረሰላማ፣ ያለምጌጥ ያረጋል እና ፍታው ዘርዬ ይሳተፋሉ።
ከቀኑ 8 ሰዓት ከ15 በግማሽ ማራቶን ወንዶች ጀማል ይመር፣ ንብረት መላክና ፀጋዬ ኪዳኑ የሚወዳደሩ ይሆናል።
ለሻምፒዮናው ውድድር አትሌቶቹ ለሶስት ሳምንታት ዝግጅት ማድረጋቸውን ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።