የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪን ጎበኙ - ኢዜአ አማርኛ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪን ጎበኙ

አዲስ አበባ፤ መስከረም 19/2016(ኢዜአ)፡- የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪን ጎበኙ።
በመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪ ናዝሬት ሸራ እና ልብስ ስፌት ፋብሪካ በሚል በ1980 ዓ.ም የተመሠረተ ሲሆን፤ የመከላከያ ሠራዊቱን የትጥቅ መያዣ እና አልባሳት አዘጋጅቶ በማስታጠቅ የረጅም ጊዜ ልምድ ያካበተ ኢንዱስትሪ ነው።
የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪ በአሁኑ ጊዜም በስሩ የሽመና እና የሹራብ ምርቶች ያሉትና የመከላከያ ሠራዊቱን እንዲሁም የሌሎች የፀጥታ አካላት ወታደራዊ አልባሳትን፣ ማዕረጎችን አርማዎችን እና ትጥቆችን እያመረተ እንደሚገኝ ተጠቅሷል።
ኢንዱስትሪው የደረሰበትን ቴክኖሎጂ አሁናዊ ሁኔታ እና የወደፊት የዕድገት አቅጣጫ በሚል ለዕለቱ የክብር እንግዶች ገለፃ መደረጉም ተገልጿል።
ገለፃውን ተከትሎ የክብር እንግዶቹን ጨምሮ የመከላከያ ሠራዊቱ ከፍተኛ አመራሮች የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪን የምርት ሂደቶች ተዘዋውረው መመልከታቸውን ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።