በአፍሪካ የድኅረ-ምርት የምግብ እህል ብክነትን ለመቀነስ በዘርፉ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋት ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
በአፍሪካ የድኅረ-ምርት የምግብ እህል ብክነትን ለመቀነስ በዘርፉ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋት ይገባል

አዲስ አበባ ፤ መስከረም 12/2016(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ በድኅረ-ምርት አሰባሰብ ሂደት የሚያጋጥመውን የምግብ እህል ብክነትን ለመቀነስ በዘርፉ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋት እንደሚገባ ተገለጸ።
አሁን ላይ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለረሃብ ከተጋለጠው 800 ሚሊየን ሕዝብ መካከል 278 ሚሊየኑ አፍሪካ ውስጥ ነው።
እንዲያም ሆኖ በአፍሪካ በድኅረ-ምርት የሚባክነው የምግብ ምርት ከጠቅላላው ምርት 31 በመቶ መሆኑን ነው የአፍሪካ ሕብረት መረጃ የሚያሳየው።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምግብና ሥነ-ምግብ ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶክተር አሻግሬ ዘውዱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በአፍሪካ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የድኅረ-ምርት ብክነትን መቀነስ ይገባል።
እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2014 በኢኳቶሪያል ጊኒ የፀደቀው የማላቦ ሥምምነት በአፍሪካ እ.አ.አ 2025 የድኅረ-ምርት ብክነት 50 በመቶ ለመቀነስ የታለመ እንደነበር አስታውሰዋል።
ይሁንና ሥምምነቱን በአግባቡ ተግባራዊ በማድረግ ረገድ ክፍተቶች መኖራቸውን ጠቁመው፤ ለተግባራዊነቱ የአፍሪካ አገራት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በተለይም በግብርና ዘርፍ ኢንቨስትመንትን በማስፋትና ዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመጠቀም የድኅረ-ምርት ብክነትን በእጅጉ መቀነስ እንደሚገባም ነው ምክረ-ሃሳባቸውን የጠቆሙት።
የሳሳካዋ አፍሪካ ማኅበር የስትራቴጂክ አጋርነት ዳይሬክተር ዶክተር ሜል ኦሉች በአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ብቻ በቂ አይደለም ብለዋል።
ከዚህ ጎን ለጎን የድኅረ-ምርት አሰባሰብ ብክነት ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ነው ያሉት።
በአፍሪካ ሕብረት አጠቃላይ የአፍሪካ ግብርና ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ ኮምላ ቢሲ በአፍሪካ የማላቦ ሥምምነትን ተግባራዊ ለማድረግ ብዙ መሥራት ይጠይቃል ብለዋል።
በአህጉሪቷ የሚያጋጥመውን የምግብ እጥረት ለመፍታት ምርትና ምርታማነትን ከመጨመር ባለፈ የድኅረ- ምርት አሰባሰብ ብክነትን መቀነስ ወሳኝ መሆኑንም እን
ለዚህ ደግሞ በዘርፉ ኢንቨስትመንትን ማስፋት፣ የቴክኖሎጂን አጠቃቀምንም ማሻሻልና የግብርና ልማት ሥራዎችን በጥናትና ምርምር መደገፍ እንደሚገባ ተናግረዋል።