የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትብብር ለማጠናከር እንደሚሻ ገለጸ

አዲስ አበባ፤ መስከረም 10/2016 (ኢዜአ)፦ የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(ዩኒዶ) ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ግንኙነት ይበልጥ ማጎልበት እንደሚፈልግ የድርጀቱ ዳይሬክተር ጀነራል ገርድ ሙለር አስታወቁ።

ድርጅቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤው በሕዳር ወር 2023 በአዲስ አበባ እንደሚያካሄድም ገልጿል።

78ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ በኒውዮርክ በመካሄድ ላይ ነው።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከጉባኤው ጎን ለጎን ከተመድ የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(ዩኒዶ) ዳይሬክተር ጀነራል ገርድ ሙለር ጋር ተወያይተዋል።

ዳይሬክተር ጀነራሉ ዩኒዶ የኢትዮጵያን የልማት ፕሮጀክቶች ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑንና የኢትዮጵያ ሰላም፣ መረጋጋትና ልማት ቀዳሚ ትኩረቶች እንደሆኑ ገልጸዋል።

ገርድ ሙለር እ.እ.አ በሕዳር ወር 2023 ድርጅቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤ በአዲስ አበባ እንደሚያካሂድ ለአቶ ደመቀ ገልጸውላቸዋል።

አቶ ደመቀ ዳይሬክተር ጀነራሉ በግላቸው እያደረጓቸው ላሉ ጥረቶች ምስጋናቸውን አቅርበው ኢትዮጵያ ከዩኒዶ ጋር ጠንካራ ግንኙነት እንዲኖራት ትፈልጋለች ብለዋል።

በተጨማሪም አቶ ደመቀ ከጉባኤው ጎን ለጎን ከአውሮፓና መካከለኛው ምስራቅ አገራት መንግስታት ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ውይይት ማድረጋቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም