የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ይካሄዳሉ - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ይካሄዳሉ

አዲስ አበባ ግንቦት 14/2015 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የሶስተኛ ቀን ውሎ ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ።
ፋሲል ከነማ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት ላይ ይጫወታሉ።
በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ፋሲል ከነማ በ37 ነጥብ 5ኛ ሲሆን ሲዳማ ቡና በ30 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ፋሲል ከነማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች ሶስቱን አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል።
ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በአንጻሩ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ በሁለቱ ተሸንፏል።
ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ ፋሲል ከነማ 4 ለ 2 ማሸነፉ የሚታወስ ነው።
በሌላኛው የ25ኛ ሳምንት የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ-ግብር ወልቂጤ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ወልቂጤ ከተማ በ29 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ድሬዳዋ ከተማ በ30 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ወልቂጤ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል።
ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በሶስቱ ተሸንፏል።
ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ያደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት መጠናቀቁ ይታወሳል።
በተያያዘም ትናንት በተደረጉ የ25ኛ ሳምንት የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሀዲያ ሆሳዕና ባህር ዳር ከተማን እንዲሁም የሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወላይታ ድቻን በተመሳሳይ 2 ለ 1 አሸንፈዋል።