ማስተር ካርድ ፋውንዴሽን ለሁለተኛው ዙር የኢትዮጵያ ፕሮግራም ከ630 ሚሊዮን ዶላር በላይ አጸደቀ

448

አዲስ አበባ መጋቢት 23/2015(ኢዜአ) ማስተር ካርድ ፋውንዴሽን ለሁለተኛው ዙር የኢትዮጵያ ፕሮግራም 630 ሚሊዮን ዶላር በላይ ማጽደቁን የስራና ክህሎት ሚኒስቴር አስታወቀ።

የፋውንዴሽኑ ፕሬዝዳንት ሪታ ሮይና ሌሎች የስራ አመራር ቦርድ አባላት ባለፉት አራት ቀናት በኢትዮጵያ የፕሮግራም ግምገማ ሲያካሂዱ መቆየታቸውን የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገልጸዋል።


 

በዚሁ መሰረት ሁለተኛው ዙር የኢትዮጵያ ፕሮግራም 630 ሚሊዮን ዶላር በላይ ማጽደቁን ሚኒስትሯ አመልክተዋል።

የጸደቀው ገንዘብ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ የፋይናንስ ተደራሽነትን ማረጋገጥ የሚያስችል የብድር አገልግሎት ለማቅረብ፣ ቴክኒክና ሙያ ተቋማትን በስራ ፈጣሪነት አስተሳሰብ ለመቅረጽ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።

በተጨማሪም ገንዘቡ ለስራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም ለተለያዩ ተግባራት ለቀጣይ ሶስት ዓመታት የሚውል ነው ብለዋል።


 

ፋውንዴሽኑ አካታችና ፍትሐዊ ዓለም ለመፍጠር፣ ትምህርትን ለማስፋፋት፣ ለወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠርና የፋይናንስ አካታችነትን የማስተዋወቅ ተልዕኮ ያለው መሆኑን ነው ሚኒስትሯ ያመለከቱት።

ከፋውንዴሽኑ የቦርድ አመራሮች ጋር በርካታ አገራዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች እንዲሁም ፋውንዴሽኑ ላለፉት በርካታ ዓመታት በኢትዮጵያ ያከናወናቸውን ተግባራትና የተጫወተው ሚና ላይ ዝርዝር ምልከታ መደረጉን ሚኒስትሯ ልጸዋል


 

በወጣቶች የፈጠራ ችሎታ እና ስራ ፈጣሪነት አምኖ የበርካቶችን ሕልም ለመፍታት ፋውንዴሽኑ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ ይገኛል ብለዋል።

በኢትዮጵያ የትምህርት፣ የፋይናንስ አገልግሎትና የክህሎት ስልጠና ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም በርካቶች ከሕልማቸው ጋር እንዲገናኙ ፋውንዴሽኑ እያደረገ ያለውን እገዛ ሚኒስትሯ አድንቀዋል።

ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ኢትዮጵያ የጀመረቻቸውን የዘላቂ እድገት የለውጥ ሂደቶች ላይ ማብራሪያ መስጠታቸውን በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ያሰፈሩት መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም