ኢትዮጵያና ላቲቪያ የውሃ ሀብት አስተዳደርን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች በትብብር ለመስራት ተስማሙ - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያና ላቲቪያ የውሃ ሀብት አስተዳደርን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች በትብብር ለመስራት ተስማሙ

አዲስ አበባ መጋቢት 19/2015(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያና ላቲቪያ የውሃ ሀብት አስተዳደርን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች በትብብር ለመስራት መስማማታቸው ተገልጿል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአውሮፓና አሜሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን ከላቲቪያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስተር የፖለቲካ ዳይሬክተር ቢሮ ረዳት ዋና ፀሐፊ አንዜጂስ ቫይሉምሰንስ ጋር ተወያይተዋል።
ውይይቱ ሁለቱ አገራት በሁለትዮሽና በባለ ብዙ ወገን የትብብር መስኮች ያላቸውን ግንኙነት ማጠናከር ላይ ያተኮረ መሆኑን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ አመልክቷል።
አምባሳደር እሸቴ ለቫይሉምሰንስ ስለ ሰላም ሂደቱ፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብና ሌሎች ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
“ላቲቪያ በአውሮፓ ሕብረትና ባልቲክ ባህር ቀጠና ወሳኝ ሚና የምትወጣ አገር ናት” ብለዋል።
ኢትዮጵያና ላቲቪያ ያላቸውን ግንኙነት ለማሳደግ ተቀራርበው መስራት እንደሚኖርባቸውም ነው አምባሳደሩ ያመለከቱት።
ሁለቱ አገራት በውሃ ሀብት አስተዳደር፣ በአየር ትራንስፖርት አገልግሎት፣ በትምህርት፣ በኢንፎርሜሽና ኮምዩኒኬሽን ቴክኖሎሎጂ፣ በግብርና፣ በቱሪዝምና በሌሎች ቁልፍ የሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ በትብብር ለመስራት ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።
የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል፣ ሰላምና ደህንነት፣ በስደተኞችና ሌሎች የጋራ ጠቀሜታ ባላቸው ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ በቅርበት ለመስራት ቁርጠኛ እንደሆኑ መግለጻቸውም ተገልጿል።
ኢትዮጵያና ላቲቪያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ2008 ነው።