ወደ ተሟላ ሰላም ለመሄድ በርካታ ሥራ መሥራት ያስፈልጋል-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ

334

አዲስ አበባ መጋቢት 19/2015 (ኢዜአ)፦ወደ ተሟላ ሰላም ለመሄድ በርካታ ሥራ መሥራት ያስፈልጋል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ማብራሪያና ምላሽ እየሰጡ ነው።

ዛሬ እየተካሔደ በሚገኘው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 11ኛው መደበኛ ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደተናገሩት አሁን ላይ ሰላምን በተመለከተ ከዛሬ ስድስት ወር የተሻለ ሁኔታ አለ ብለዋል።


 

ወደተሟላ ሰላም ለመሄድ በርካታ ሥራ መሥራት ያስፈልጋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነገር ግን አንድ ርምጃ ወደፊት የወሰደ ሥራ ተሠርቷል ሲሉም ገልጸዋል።

ባለፉት 50 እና 60 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረው ፖለቲካ የመተላለፍ፣ የሴራ እና የጉልበት ፖለቲካ እንደነበረ ገልጸው “ሰላም አስፈላጊ ነው ብለን በጽኑ እናምናለን፣ ሰላም እንደጦርነት ጀግንነት ይፈልጋል፣ ከጦርነት ያልተናነሰ ሥራ ድካም ይጠይቃል” ብለዋል።

የረጋ ሰላማዊ ነገር እንዲሁ አይመጣም አዎንታዊ ሰላም በሀይል አይመጣም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምንጊዜም ሰላም ሲባል የአንድ ሰው ህይወት ማትረፍም ስለሆነ በዚህ ላይ መሥራት ይገባናል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም