ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነባት አገርን ለመገንባት ለጸረ ሙስና ትግሉ ውጤታማነት ሁሉም ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነባት አገርን ለመገንባት ለጸረ ሙስና ትግሉ ውጤታማነት ሁሉም ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል
![](/documents/42135/0/9+%289%29.png/b89a8777-c4c3-0e5c-237e-ab48746569b3?version=1.0&t=1679479719324&download=true)
አዲስ አበባ መጋቢት 13/2015 (ኢዜአ) ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነባት አገርን ለመገንባት ለጸረ ሙስና ትግሉ ውጤታማነት ሁሉም ኃላፊነቱን እንዲወጣ የፌደራል ሥነምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ጥሪ አቀረበ።
ኮሚሽኑ በፌዴራል ተቋማት ስር ለሚገኙ ለስነ ምግባር እና የፀረ-ሙስና ክፍል፣ ለውስጥ ኦዲት አገልግሎት፣ለሕግ አገልግሎት እና ለተቋማት ለውጥ ስራ አመራር ኃላፊዎች ያዘጋጀው ስልጠና ዛሬ በቢሾፍቱ ተጀምራል።
በስልጠናው የዩኒቨርስቲዎች ሥነምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ክፍል ኃላፊዎችም ተሳትፈዋል።
የፌደራል ሥነምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ወዶ አጦ ሙስና ኢትዮጵያ ከተጋረጡባት ዋንኛ ችግሮች መካከል አንዱ መሆኑንና እየቀያየረ ያለው ሙስና የኢኮኖሚ እድገትን በመግታት ፣አንድነትን በማናጋት ስርዓተ መንግስቱን ለመናድ አደጋ የሚጋርጥ መሆኑን ገልጸዋል ።
ችግሩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ የደህንነት ስጋት በመሆኑ መንግስት ሙስናን ለመታገል ብሔራዊ ኮሚቴ አዋቅሮ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በመሆኑም ጠንካራ ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነባት አገር ለመገንባት የተጀመረው የፀረ-ሙስና ትግል ውጤታማ እንዲሆን ሁሉም የበኩሉን ኃላፊነት ሊወጣ እንደሚገባ ተናግረዋል።
ሁሉም የፀረ-ሙስና ትግሉ ባለቤት መሆን እንዳለበትም ነው ምክትል ኮሚሽነሩ ያመለከቱት።
ዛሬን ጨምሮ ለሶስት ቀናት በሚቆየው ስልጠና ከ260 በላይ የፌደራል ተቋማት የስራ ኃላፊዎች መሳተፋቸው ተገልጿል።