የክልሉን ሰላም ለማወክ በህወሃት የሚደረገውን ሴራ በንቃት ማክሸፍ ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
የክልሉን ሰላም ለማወክ በህወሃት የሚደረገውን ሴራ በንቃት ማክሸፍ ይገባል

ሐዋሳ፣ ሐምሌ 15/2012 (ኢዜአ) ለረጅም ዘመናት የቆዩ የአደረጃጀት፤የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ ጥረት እየተደረገ ባለበት ወቅት በህወሃት ተልዕኮ አስፈጻሚዎች በኩል የክልሉን ሰላም ለማወክ የሚደረገውን ሴራ በንቃት ማክሸፍ እንደሚገባ የደቡብ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።
የጽሕፈት ቤት ኃላፊው አቶ ጥላሁን ከበደ ሃዋሳ ላይ እየተካሔደ ባለው የክልሉ የብልጽግና ፓርቲ የአመራሮች መድረክ ላይ እንደተናገሩት ህወሃቶች የክልሉን ሰላም ለማወክ ለዓላማቸው ማስፈጸሚያ የሚሆኑ የአመራርነት ሚና ያልገባቸውን አካላት እየተጠቀሙ ነው።
"በመሆኑም ለለውጥ አደናቃፊ ሃይል መጋለቢያ ፈረስ መሆን አይቻልም" ያሉት አቶ ጥላሁን "በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች በአመለካከትም ሆነ በተግባር አንድ ላይ በመሆን የለውጥ ሂደቱን ውጤታማ ማድረግ የሚያስችል ቁመና ላይ የደረሰ አመራር ለመፍጠር በትኩረት ይሠራል"ብለዋል።
"ህወሐት እያካሄደ ያለው የሴራ ፖለቲካና እኩይ ድርጊት ለትግራይ ህዝብም ጭምር ጠላት መሆኑን ማሳያ ነው" ያሉት አቶ ጥላሁን "በሃገሪቱ ዘርፈ ብዙ አፈናዎችን በማድረሱ የኢትዮጵያ ህዝብ አልፈልግም ብሎ የተፋው ህወሐት መቀሌን ምሽግ ቢያደርግም ሃገሪቱን መልሶ መቀመቅ ላይ ለመክተት የሴራ ፖለቲካና እኩይ ድርጊት እያካሄደ ነው" ብለዋል፡፡
"በህዝብ ግፊት የመጣውን ለውጥ ለመቀልበስ በሃገራችንና በክልላችን ከውጭ ሃይሎች ጋር በመመሳጠር ሁከትና ብጥብጥ ለማስነሳት እያካሄደ ያለው የሴራ ፖለቲካ ባህሪ፤ተግባርና አደረጃጀቱን ማወቅና መመከት የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ ነን" ብለዋል፡፡
በክልላችን የህዝቦችን አንድነት በመሸርሸር የተጀመረውን የልማት ሂደት ወደ ኋላ ለመመለስ እየተደረገ ያለውን ሴራ በመረዳት ለመመከትና ለማክሸፍ በክልሉ በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች በጠንካራ ቁመና ላይ ሊቆሙ እንደሚገባም አቶ ጥላሁን አሳስበዋል።
"የብጥብጥና የሁከት የሴራ ፖለቲካ ዋና ጠንሳሽ ህወሐት መሆኑን በአግባቡ በመረዳት ህብረተሰቡ እኩይ ዓላማቸውን እንዲረዳ ማድረግና መታገል ይጠበቃል" ያሉት ኃላፊው በክልሉ በተለያዩ አከባቢዎች እጃቸውን በማስገባት ህዝቡን ለማበጣበጥ እየሰሩ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
"የህወሃትን ሴራ የማጋለጥ ሂደት ከትግራይ ህዝብ ጋር የሚገናኝ አይደለም" ያሉት አቶ ጥላሁን ህወሀት እየፈጸመ ያለው የሴራ ፖለቲካ ከትግራይም ባለፈ ለሁሉም ክልል ህዝቦች የጠላትነት ተግባር በመሆኑ ነጥሎ መታገል እንደሚገባ አመልክተዋል።
"ሴራቸውን ለማሳካት በየአካባቢው በተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲና በፌዴራሊስት ሃይሎች ስም ኢ-መደበኛ አደረጃጀት በማቋቋም ከፍተኛ ነውጥ ለማስነሳት እየሰሩ ነው" ብለዋል፡፡
የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ርስቱ ይርዳው በበኩላቸው "ህዝብ የሚፈልገውን ሠላምና ልማት ለማረጋገጥ ፓርቲው በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸው በዚህ ሂደት እኩይ ዓላማ ያላቸው አካላትን ሴራ ለማክሸፍና የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ ይሰራል" ብለዋል።
በዚህ ሂደት ወንጀል ከሰሩ በኋላ ብሄርን መደበቂያ የሚያደርጉ አካላት ሊበቃላቸው እንደሚገባም አአሳስበዋል።
በክልሉ የሁሉም ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ከፍተኛ አመራሮች እየተሳተፉበት የሚገኘው የብልጽግና ፓርቲ የአመራሮች መድረክ በሐዋሳ ከተማ በመካሄድ ላይ ነው፡፡