በዛሬው ዕለት ብቻ ተጨማሪ 100 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ሲገኝባቸው የ1 ሰው ህይወት አልፏል

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 20/2012(ኢዜአ) በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓት በተደረገ 4950 የላቦራቶሪ ምርመራ ተጨማሪ 100 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ እንደተገኘባቸውና 1 ሰው ህይወት እንዳለፈ የጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ አስታወቁ።

በዚህም እስካሁን በሀገሪቱ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 831 ደርሷል።

ሚኒስትሯ እንደገለፁት ቫይረሱ እንደተገኘባቸው የተረጋገጠው እድሜያቸው ከ3 እስከ 70 ዓመት ነው፡፡

በምርመራ ከተረጋገጠው 53 ወንድና 47 ሴቶች ሲሆኑ 99 ሰዎች ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ 1 ሰው የቡሪንዲ ዜጋ መሆኑን ዶክተር ሊያ ተናግረዋል።

ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች 94 ሰዎች ከአዲስ አበባ ሲሆኑ፣ 34 ሰዎች በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት ያላቸው፣ 60ዎቹ ደግሞ የውጭ ሀገር ጉዞ ታሪክ ወይም በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት የሌላቸው ናቸው ተብሏል።

አንድ ሰው ከትግራይ ክልል የውጭ ሀገር ጉዞ ታሪክ ያለውና በለይቶ ማቆያ ውስጥ ያለ፣ 2 ሰዎች ከሶማሌ ክልል ሁሉም የውጭ ሀገር ጉዞ ታሪክ ያላቸውና በለይቶ ማቆያ ያሉ፣ እንዲሁም 3 ሰዎች ከኦሮሚያ ክልል ሲሆኑ 1 ሰው በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት ያለውና 2ቱ የውጭ ሀገር የጉዙ ታሪክና በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት የሌላቸው ናቸው፡፡

ሚኒስትሯ አክለውም በተጓዳኝ ህመም ምክንያት ህክምና ላይ የነበሩ የ70 ዓመት ዕድመሜ ያላቸው ሴት በኮሮና ቫይረስ በሽታ በተደረገ የምርመራ ናሙና ከተወሰደ በኋላ የምርመራ ውጤት ሳይደርስ ህይወታቸው አልፏል ብለዋል።

በምርመራ ውጤትም ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ስለተረጋጋጠ በአጠቃላይ በቫይረሱ ህይወታቸው ያለፉ ሰዎች ቁጥር 7 ደርሷል።

ባጋጠመው የሞት አደጋ የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የተሰማቸውን ሀዘን እየገለጹ ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን ተመኝተዋል።

በአጠቃላይ ቫይረሱ ተገኝቶባቸው በለይቶ ህክምና ውስጥ ያሉ 631 ሰዎች ናቸው።

በሌላ መልኩ በትናንትናው ዕለት 10 ተጨማሪ ሰዎች ከአዲስ አባበ ከበሽታው ያገገሙ ሲሆን ቁጥሩም 191 ደርሷል።

አንድ ሰው በጽኑ ህክምና ክፍል ክትትል እየተደረገለት መሆኑም ታውቋል።

የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የኮሮና ቫይረስ ስርጭት መጨመርን ከግንዛቤ በማስገባት ህብረተሰቡ ጥንቃቄዎችን አዘውትሮ እንዲተገብር አሳስበዋል፡፡

እስካሁን በኢትዮጵያ አጠቃላይ 96,566 የላቦራቶሪ ምርመራ ተከናውኗል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም