በአዲስ አበባ ከተማ ለ300 ግለሰቦች ለኢድ አልፈጥር በዓል ማክበሪያ በጎች ተበረከቱ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 14/2012 (ኢዜአ) በአዲስ አበባ ከተማ ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ለ300 ግለሰቦች ለኢድ አልፈጥር በዓል ማክበሪያ በጎች ተበረከቱ። 

በክፍለ ከተማው አቅም ለሌላቸው የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች የተበረከቱት በጎች ከ880ሺህ ብር በላይ ወጪ እንደተደረገባቸው ዛሬ በተካሄደው የርክክብ ሥነ ሥርዓት ተገልጿል።

የክፍለ ከተማው ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አደም ኑሪ የክፍለ ከተማውን የንግድ ማህበረሰብና ግለሰቦች በማስተባበር የእምነቱ ተከታዮች በዓሉን በየቤታቸው በደስታ እንዲያከብሩ ስጦታው ተበርክቷል ብለዋል።

አስተዳደሩ ላቀረበላቸው ጥሪ አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ስጦታውን ላደረጉ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።

በአስተዳደሩ በኮቪድ ወረርሽኝ ምከንያት ችግር ውስጥ ለወደቁ ከ8ሺህ በላይ ለሚሆኑ ቤተሰቦች የምግብና የንጽህና መጠበቂያ ቁሳቁስ ድጋፍ እንደተደረገም ገልጸዋል።

በተጨማሪም ከ4ሺህ በላይ ለሚሆኑ ቤተሰቦች እስከ ሦስት ወራት የሚደርስ ድጋፍ ከሚያደርጉ ቤተሰቦች ጋር ማስተሳሰሩን አቶ አደም አስታውቀዋል።

ወረርሽኙን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ማህበራት፣ በጎ ፈቃደኞችና ቤተ እምነቶች የቤት ኪራይ በመቀነስና ህንጻቸውን መለገስ 24 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ማድረጋቸውን ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልፈታ የሱፍ ድጋፉ የንግዱን ማህበረሰ በመሳተፍ መሰባሰቡንና እርስ በርስ የመደጋገፍ ባህልን እንዳንጸባረቀ ነው ብለዋል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የማህበራዊ ጉዳይ ዘርፍ ቋሚ ኮሚቴ ተወካይ ወይዘሮ ሰሚራ ሱልጣን

ድጋፉ ወቅቱ እርስ በእርስ መተሳሰብና መደጋገፍ እንደሚያስፈልግ ያመለከተ መሆኑን ገልጸው፤በክፍለ ከተማው የተደረገው ድጋፍም ይህንኑ እንዳሳየ ገልጸዋል።

ድጋፉን ላስተባበሩ አካላት የእውቅና ሰርተፊኬት ተበርክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም