የረመዳን ጾም ነገ ይጀመራል - ኢዜአ አማርኛ
የረመዳን ጾም ነገ ይጀመራል

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 15/2012 (ኢዜአ) የረመዳን ፆም በመላው የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በነገው ዕለት ይጀመራል።
ከአምስቱ የእስልምና መሰረቶች መካከል የረመዳን ፆም አንዱ ሲሆን ሃጅ ማድረግ፣ በአላህና መልእክተኛው ማመን፣ ሰላት መስገድና ዘካ መስጠት ይጠቀሳሉ።
የረመዳን ፆም በእስላማዊ የጊዜ ቀመር በየዓመቱ 9ኛው ወር ላይ በመላው የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ ከሚበላና የሚጠጣ ነገር በመከልከልና ከመጥፎ ተግባራት በመራቅ ፆሙ ይከናወናል።
በእምነቱ ተከታዮች ''ታላቁ ወር'' ተብሎ በሚጠራው በዚህ ወር ከፆም በተጨማሪ ቁርአን በመቅራት (በማንበብ)፣ ለፀሎትና ዚክር ከሌላው ጊዜ የተለየ ትኩረት በመስጠት እንዲሁም ለተቸገሩ መለገስ የተወደደና ከፈጣሪያቸውም ዘንድ የሚከፈለው መንፈሳዊ ዋጋ ላቅ ያለ መሆኑ ይታመናል።
በመሆኑም በዚህ ወር ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እነዚህን ተግባራት በመፈፀም ከፈጣሪያቸው ምህረትን ለማግኘት ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ተቀዳሚ ሙፍቲ ሃጂ ኡመር እንድሪስ ተናግረዋል።
የዘንድሮውን የረመዳን ፆም በማስመልከት በሰጡት መግለጫም ረመዳን የምህረት ወር መሆኑን በመረዳት ፀሎትን ማጠናከርና በጎ ስራዎችን እንዲያበዙ አሳስበዋል።
በተለይ አቅመ ደካሞችንና ችግረኞችን መርዳት እንደሚገባና የኮሮና ቫይረስን ለመከላከል በሚመለከታቸው አካላት የሚሰጠውን ትእዛዝ ማክበር ያስፈልጋል ብለዋል።
የዘንድሮው የረመዳን ፆም በአመተ ሂጅራ አቆጣጠር ለ1 ሺህ 440ኛ ጊዜ መሆኑ ነው።