በአዲስ አበባ የታክሲ ትራንስፖርት ታሪፍ ማሻሻያ ተደረገ - ኢዜአ አማርኛ
በአዲስ አበባ የታክሲ ትራንስፖርት ታሪፍ ማሻሻያ ተደረገ
አዲስ አበባ ፣ሚያዚያ 2/2012 (ኢዜአ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ቢሮ በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት የታክሲ ትራንስፖርት ታሪፍ ማስተካከያ ማድረጉን አስታወቀ።
በተስተካከለው ታሪፍ መሰረት ዝቅተኛው 3 ብር ሲሆን ከፍተኛው ደግሞ 12 ብር ከ50 ሣንቲም ሆኗል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ ኮማንደር አህመድ መሐመድ በሰጡት መግለጫ ወረርሽኙን ለመግታት የወጣው መመሪያ በዋናነት በተሽከሪካሪዎች የመጫን አቅምና በታሪፍ ላይ ያተኩራል።
በመመሪያው መሰረት ታክሲዎች ከመጫን አቅማቸው 50 በመቶ ብቻ እንዲጭኑ ይገደዳሉ።
መመሪያውን ተላልፎ የተገኘ አሽከሪካሪ የ5 ሺህ ብር ቅጣት የሚጠብቀው ሲሆን በወንጀልም ተጠያቂ እንደሚሆን ኮማንደሩ አስረድተዋል።
ተሳፋሪዎች እጥፍ ታሪፍ ከፍለው እንዲጓዙ በመመሪያው መደንገጉንም ኮማንደር አህመድ ገልጸዋል።
በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ ሕገ ወጥ ተግባራት ሲያጋጥሙ ጥቆማ የሚሰጥበት የጥሪ ማዕከል መዘጋጀቱንም ተናግረዋል።
በተጨማሪም በታክሲ አገልግሎት የሚያጋጥሙ ሕገ ወጥ ተግባራትን ተከታትለው እርምጃ የሚወስዱ ከ100 ያላነሱ ሞተር ሳይክሎች መሰማራታቸውን ጠቁመዋል።
ኅብረተሰቡ ከመንግሥት ጎን በመሆን ሕገ ወጦችን በማጋለጥ መብቱን እንዲያስከብርም ኮማንደር አህመድ ጠይቀዋል።
የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝነን ለመከላከል ሲባል በአዲስ አበባ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከሪካሪዎች ከመጫን አቅማቸው ከፊሉን በመቀነስ አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉ ይታወቃል።