ቀጥታ፡

“ ቃልና እብሪትን ያፈራረሰው ድል”

በእንግዳውከፍያለው-ከባህርዳርኢዜአ

“ሞኝና ወረቀት የያዘውን አይለቅም” ይላሉ አባቶች። ወረቀት ላይ ተከትቦ የሚቀመጠው ደግሞ “ቃል” ነው። ቃላት ተገጣጥመው ዓረፍተ ነገር፣ አንቀጽ…እየመሰረቱ ይቀጥላሉ። ቃል በእኛ ሃገር ክቡር ነው። ቃል ያስገድላል ። ቃል ከሞት አፋፍ ያድናል ። “የተናገሩት ከሚጠፋ የወለዱት ይጥፋ” አይደል የሚለው ያገሬ ሰው።

ለዚህም ይመስላል “ኢይጻ አቢይ ነገር እም አፉክሙ” ይላል ታላቁ መጽሃፍ። ትርጉሙም “ክፉ ቃል ከአፍህ አይውጣ” የሚል ነው። አሁን በአገራችን እየተስተዋለ የሚገኘው የእርስ በርስ መጓተት የተከሰተው ለብዙ ዓመታት ሲቀነቀኑ በመጡ ቃላት ላይ የተመሰረተ ነው። መንግስትም የጥላቻ ንግግርን ለማስወገድ አዋጅ እስከማውጣት አስገድዶታል።

ለአድዋ ጦርነት መከሰትም መነሻው ቃል ነው። እንዴት አንዲት ቃል የአድዋን ጦርነት ልትቀሰቅስ ትችላለች? የሚል ሃሳብና ክርክር መነሳቱ አይቀርም። መከራከሩም ሆነ ሃሳብ ማንሳቱ መልካም ነገር ነው። በሃሳቡ ተከራክሮ የተለየ አቋም መያዝም የዴሞክራሲ መገለጫ በመሆኑ የጽሁፉን መነሻ አያደበዝዘውም ።

ለአድዋ ጦርነት እንደ መነሻ የሚጠቀሰው አንቀጽ 17 ነው እየተባለ ሲነገር በተደጋጋሚ ሰምተናል። መስማት ብቻ ሳይሆን በተለያዩ መጻህፍትም አንብበናል ። ትረካዎችን አዳምጠናል ። ከአባቶቻችን ሲወርድ ሲዋረድ በመጣው አፈ ታሪክም አድምጠናል…።

በዚህ አንቀጽ ውስጥ ያን ያህል ደም መፋሰስ ያስከተለው ጦርነት እንዲካሄድ ምክንያት መሆኑ ብዙዎቻችን እናምናለን ። ለጦርነቱ ምክንያት የሆነው ግን በአንቀጹ ያለው ገጽ፣ አንቀጽ ወይም ዓረፍተ ነገር ሳይሆን ቃል ነው። አዎ ! ቃል ነው ። አይደለም የሚል ካለ ደግሞ በማስረጃ መሞገት መብቱ የተጠበቀ ነው።

ነገሩ እንዲህ ነው። እንዴት? አትሉኝም። የውጫሌ ውል አንቀጽ 17 በጣሊያንኛ የተጻፈው ትርጉም “ኢትዮጵያ ከአውሮፓ መንግሥታት ጋር ማድረግ የምትፈልገውን ግንኙነት በኢጣሊያ መንግስት በኩል ማድረግ አለባት” ይላል።

በአማርኛው የተጻፈው ደግሞ “ኢትዮጵያ ከአውሮፓ መንግሥታት ጋር ማድረግ የምትፈልገውን ግንኙነት በኢጣሊያ መንግሥት በኩል ማድረግ ትችላለች” የሚል ነው።

በጣሊያንኛ የተጻፈው አንቀጽ 56 ፊደላት ፣ 12 ቃላትና አንድ ዓረፍተ ነገርን ያካተተ ሲሆን በአማርኛ የተጻፈው ደግሞ በአንድ ፊደል ይበልጣል። የተጻፉት ቃላትም ከማሰሪያ አንቀጹ ውጭ ሌላው ተመሳሳይ ነው።  ከዚህ ውስጥ ለአድዋ ጦርነት መንስኤ የሆነው የመጨረሻው ቃል መለያየት ብቻ ነው።

ይህም በጣሊያንኛው “አለባት” የሚል ሲሆን በአማርኛው ደግሞ “ትችላለች” የሚል በመሆኑ ነው። በጣሊያንኛውና በአማርኛው የተለያየ ትርጉም በመስጠቱ የጦርነት መንስኤ ለመሆን በቅቷል።

በጣሊያንኛ የተገለጸው “አለባት” የሚለው የዓረፍተ ነገሩ ማሰሪያ ቃል ግዴታን የሚያመላክት ሲሆን “ትችላለች” የሚለው ግን ኢትዮጵያን የሚያስገድድ ሳይሆን ከፈለገች ብቻ ማድረግ እንደምትችል የሚያመላክት ነው። ይህ ማለት ኢትዮጵያ ከፈለገች ጣሊያንን ተጠቅማ ዲፕሎማሲያዊ ስራዋን ማሳለጥ ትችላለች ። ካልፈለገች ደግሞ በራሷ ከፈለገችው አገር ጋር ያለማንም ጣልቃ ገብነትና አስገዳጅነት ዲፕሎማሲያዋን ማስቀጠል ትችላለች የሚል ነው።

 የቃላት ልዩነት ትልቅ የትርጉም ልዩነት በማምጣቱ የጥቁር ህዝቦች ነጻነት የተበሰረበትን ታላቁ የአድዋ ጦርነት እንዲነሳና በኢትዮጵያዊያን ድል አድራጊነት እንዲጠናቀቅ አድርጓል ።

የትርጉም ልዩነቱ የታወቀው ደግሞ የአጼ ሚኒሊክ ለአውሮፓ ሃያላን አገራት ደብዳቤ ይልካሉ ። ደብዳቤ ከተላከላቸው መካከል የእንግሊዝና የጀርመን መንግስታት ይህ ደብዳቤ መምጣት ያለበት በስምምነታችሁ መሰረት በጣሊያን በኩል በመሆኑ አንቀበለውም ብለው መለሱት።

ለዚህም የጣሊያን መንግስት ቀድሞ ለአውሮፓ ነገስታት ኢትዮጵያ ከእንግዲህ በስሬ ለመሆን ተስማምታለች ብሎ በጣሊያንኛ ቋንቋ የተጻፈውን የውጫሌ ስምምነትን  አሳውቆ ስለነበር መሆኑ ይታወቃል ። አንቀጽ 17 ላይ ያለው በጣሊያንኛ የተጻፈው “አለባት” የሚለው አስገዳጅ ቃል በመኖሩ ምክንያት አድርገው ነው ያልተቀበሉት።

ለአጼ ሚኒልክም በውጫሌ በፈረሙት ስምምነት በጣሊያንኛውና በአማርኛ የተጻፈው ማሰሪያ አንቀጽ ቃል ላይ ልዩነት እንዳለው ጣሊያንኛ ቋንቋ ጠንቅቀው የሚያውቁት ፕሮፌሰር አፈወርቅ ገብረ ኢየሱስ አረጋገጡላቸው። የትርጉም ልዩነት መኖሩንም ሆነ ደባ የተፈጸመባቸው መሆኑን አላወቁም ነበር። “ቁጭ ብለው የሰቀሉት ቁሞ ለማውረድ ይከብዳል” የሚለው አባባል የገጠማቸው አጼ ሚኒሊክ የውጫሌን ውል ውድቅ ማድረጋቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ መልሰው ለአውሮፓ ታላላቅ ነገስታት ጻፉ።

የጣሊያን መንግስት በአውሮፓውያን ነገስታት ፊት ክብሬ እንዴት በጥቁር ይዋረዳል በማለት መልዕክተኛ ላከ ። አጼ ሚኒሊክና እቴጌ ጣይቱም የትርጉም ልዩነት ያመጡ ቃላቶችን ለማስታረቅ ከጣሊያኑ መልዕክተኛ ጋር ተደጋጋሚ ድርድር አድርገዋል።

ነገር ግን የጣሊያን ልዑካን ኢትዮጵያን ማንበርከክና በቅኝ ግዛቱ ስር ለማድረግ ካለው ፍላጎት በመነሳት ለማስተካከል ፈቃደኛ አልነበሩም። ጦርነቱ እንደማይቀር ቀድሞ የገባቸው እቴጌ ጣይቱም  “እኔ ሴት ነኝ ጦርነት አልወድም። ይህን ስምምነት ከምቀበል ግን ጦርነትን እመርጣለሁ” በማለት የጣሊያኑን ተደራዳሪ በሃፍረት ተከናንቦ እንዲመለስ ማድረጋቸው በታሪክ ተመዝግቦ ይገኛል።

ከዛ በኋላ ነው አጼ ሚኒልክ የማይቀረውን ጦርነት ለማካሄድ ዝግጅት ማድረግ የጀመሩት። ለሁሉም ክፍለ ሀገራት ገዥዎች መልዕክት ማስተላለፍ ፣ የማዕከላዊውን ጦር ማዘጋጀት ፣ የስንቅና የመሳሪያ አቅርቦትን ማፈላለግ፣ ህዝቡን በስነ ልቦና ለማጠናከር የሚያስችሉ መልዕክቶችን ማስተላለፍ የጀመሩት ።

በሒደትም የደቡብ፣ የምስራቅ፣ የደቡብ ምዕራብና የመኽል አገር ዘማች ከአዲስ አበባ በ468 ኪሎ ሜትር ላይ ከምትገኘው ወረኢሉ ላይ ጥቅምት ወር ላይ እንዲደርስ ተወሰነ። የሰሜን ምዕራብና የሰሜን ዘማቾች ደግሞ በቀጥታ ወደ ትግራይ እንዲዘምቱ ተደርጓል።

ወረኢሉ የጦሩ መሰባሰቢያ ብቻ ሳይሆን የሰራዊቱ ቀለብ የሚሆን እህል የተከማቸባትና በየጊዜው እየተዘጋጀ ወደ ጦር ሜዳ የሚላክባት የሎጅስቲክ ማዕከል ሆና እንዳገለገለች የአማራ ክልል የጥንታዊት ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ ዳኝነት አያሌው ይገልፃሉ ።

የንጉሱ ትእዛዝ የተቀበለው የገበሬ ተዋጊ ሴት ወንድ፣ ህጻን አዛውንት፣ የአካል ጉዳተኛ ጎበዝ ሳይለይ ሁሉም ጉዞ ወደ አድዋ ተመመ። ከአድዋ ጦርነት ቀድሞ የተካሄደውን የአምባልጌና መቀሌ ጦርነት የኢትዮጵያ ጦር በድል ማጠናቀቁ ይታወሳል።

የጣሊያን መንግስት ከ1850ዎቹ ጀምሮ ወንጌልን ለመስበክ፣ ንግድን ለማስፋፋት፣ ለዲፕሎማሲና ሌሎች ምክንያቶች በርካታ የጣሊያን መንግስት ሰላዮች ገብተው ከንጉሰ ነገስት እስከ መሳፍንቱ ድረስ ወዳጅነት መስርተው ነበር ሲሉ የሚገልፁት ደግሞ በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ተመራማሪ የሆኑት ፕሮፌሰር ተሾመ ሲሻኝ ።

እንደ ሽጉጥ ያሉ ቀላል መሳሪያዎችን፣ ጌጣጌጦችንና ሌሎች ዘመናዊ የመጠቀሚያ ቁሳቀሱሶችን በመስጠትም ግንኙነታቸውን  አጠናክረዋል። ንጉሰ ነገስቱን ከመሳፍንቱ ጋር ያለውን ግንኙነት ለማበላሸትም የጣሩ ነበሩ። እንዴት የጣሊያን መንግስት ኢትዮጵያን በቀላሉ ተቆጣጥሮ መግዛት እንዳለበት የማመቻቸት ስራ የሰሩት እነዚህ ሰላዮች ነበሩ። በሚኒሊክ የአመራር ጥበብ በመጨረሻ ቢከሽፍባቸውም።

ከእነዚህ ሚሽነሪዎች መካከል በግንባር የሚጠቀሰው ጁሴፔ ሳፔቶ የሚባለው የካቶሊክ መነኩሴ ነው። ለመጀመሪያ ጊዜ አሰብን ረግጦ ከአካባቢ ሱልጣን ወይም ገዥ እ.ኤ.አ በ1869 የአሰብ ወደብን በመግዛት ሩባቲኖ ለተባለው የጣሊያን የመርከብ ካምፓኒ አስተላለፈው ።

የጣሊያን ጦርም ወዲያውኑ አሰብ ላይ ሰፍሮ ምጽዋን ለመያዝ ወደ ሰሜን መስፋፋት ጀመረ። በዚህም የጣሊያን ጦር ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያዊው ራስ አሉላ አባ ነጋ ዶጋሊ ላይ ሊደመሰስ ችሏል። የጣሊያን ጦር ወደ ምጽዋ ለመስፋፋትና ኤርትራን ለመቆጣጠር ያደረገው ጥረት ጉራዕ ፣ ኩፊትና ጉንዲት ላይ ሽንፈት መከናነቡን በታሪክ ተዘግቧል።

የጣሊያን ጦር መሪ ጄነራል አልበርቶኒና የሰራዊቱ አዛዥ ጀኔራል ባራቴሪ በዓለም ላይ ዘመናዊ የተባለና የሰለጠነ 25 ሺህ ወታደር በማዘጋጀት ኢትዮጵያን ቅኝ ለመግዛት ቆርጦ ተነሳ ። ቆርጠ መነሳት ብቻ ሳይሆን የመረብ ወንዝን ተሻግሮ የትግራይን መሬት ከረገጠ ሰነባበተ ። መቀሌን አልፎ አምባላጌ ላይ በመመሸግ መላ አገሪቱን ለመቆጣጠር ቋምጧል ።

የታጠቀው መሳሪያም 60 ዘመናዊ መድፍ፣ መትረየስና ሌሎች አውቶማቲክ መሳሪያዎችን ያካተተ መሆኑ ለጦር መሪውና አዛዡ የልብ ልብ ሰጥቷቸዋል። የጣሊያን ጦር በህዳር ወር 1988 ዓ.ም አምባላጌ ላይ ተሸንፏል። የተሸነፈው ጦር ወደ መቀሌ አምርቶ እዛው ከነበረው ጦር ጋር በመቀላቀል ምሽጉን አጠናክሮ መከላከል አድርጓል።

የመቀሌን ምሽግ ለማስለቀቅ ሌላ ዘዴ ጠይቋል ። በእቴጌ ጣይቱ የጦር ጥበብና ብስለት አፍላቂነት ጣሊያን የሚጠቀምባቸው የውሃ ምንጮችን ቀድሞ በመያዝ ውሃ እንዳያገኝ ተደረገ። በውሃ ጥም ሊያልቅ የደረሰው የጣሊያን ጦር ምሽጉን ለቆ ወደ ሰሜን በመመለስ ከጣሊያን የደጀን ጦር ጋር ተቀላቅሏል።

ሃያ ዘጠኝ ሺህ ፈረሰኞችን ጨምሮ እስከ 120 ሺህ የሚገመት የኢትዮጵያ የገበሬ ሠራዊት 1 ሺህ ኪሎ ሜትርን በእግር ተጉዞ በወታደራዊ አካዳሚ የሠለጠነውን የአውሮፓ ወራሪ ጦር የካቲት 23 ማለዳ አሥራ አንድ ሰዓት አካባቢ አድዋ ላይ ገጠመ ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ታሪካዊውን የኢትዮጵያ ድል መበሰሩን  እንግሊዛዊውን የታሪክ ተመራማሪ ጆርጅ በርክሌይ “የአድዋ ጦርነትና ዳግማዊ አፄ ምኒሊክ” በተሰኘው መጽሃፉ ላይ ተዘግቧል ።

ጦርነቱ በተጀመረ ከአምስት ሰዓት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ 56ቱም የኢጣሊያ መድፎች ሙሉ ለሙሉ ተማርከዋል ። የቅኝ ገዢውን ወራሪ ሠራዊት ከመሩት ውስጥም ጄኔራል አልቤርቶኒ ሲማረክ የሠራዊቱ ዋና አዛዥ ጄኔራል ባራቴሪ ከጥቂት አጃቢዎቹና በሽንፈት ከተበታተኑ የኢጣሊያ ወታደሮች ጋር ሸሽቷል፡፡

በዚህ ድብልቅልቅ ያለ ውጊያ ከ56ቱ የኢጣሊያ መድፎች በተጨማሪ ብዙ ሺህ ቀላልና ከባድ መትረየሶች እንዲሁም የነፍስ ወከፍ ጠመንጃዎች በአሥር  ሺዎችና በመቶ ሺዎች ከሚቆጠሩ መሰል ጥይቶቻቸው ጋር በኢትዮጵያዊያን እጅ ገብተዋል ። በአጠቃላይ የተማረከው መሳሪያ ወደ አዲስ አበባ የተጓጓዘው በ500 አጋሰሶች በመጫን እንደነበር በታሪክ ተዘግቦ ይገኛል።

 “በሚኒሊክ መሪነት የተገኘው የአድዋ ድል አውሮፓውያን ለዘመናት የሰሩትን የነጭ የበላይነትና የጥቁር የበታችነት ታሪክ ያፈራረሰ ነው በማለት ፕሮፌሰር ሹመት ሲሻኝ ማብራሪያቸውን ይቀጥላሉ። በዚህም መላው አፍሪካውያንና ሌሎች በቅኝ ግዛት የተያዙ አገራት ነጭ መሸነፍ እንደሚችል አምነው ለትግል የተነሳሱበት የነጻነት ፋና ወጊ ድል ነው የኢትዮጵያ ህዝቦች ያስመዘገቡት።

ለድሉ መገኘትም ብቃት ያለው አመራርና በቂ ዝግጅት በማድረግ የተካሄደ ጦርነት በመሆኑ አንድ ቀን ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አንጸባራቂው የአድዋ ድል ሊመዘገብ ችሏል ብለዋል። የዚህ ዝግጅትና አመራር ጥበብ መሃንዲስ ደግሞ እምዬ ሚኒልክ መሆናቸውን መስክረዋል። ከፈረንሳይ ጋር ባላቸው የጠበቀ ግንኙነት እስከ 100 ሺህ የሚደርስ ቀላል መሳሪያ እንዳስገቡም አንዳንድ የታሪክ ጸሃፍት ዘግበዋል።

ከአውሮፓ መንግስታት ጋር ቅርበት የሌላቸውን የውጭ ምሁራን በመጠቀም የውጭ ሚዲያዎች ለኢትዮጵያ ትኩረት ሰጥተው እንዲዘግቡ ቀደም አድርገው መስራታቸውም ይነገራል። ለዚህም ይመስላል የአድዋ ድል ሲመዘገብ ቪቫ ሚኒሊክ፤ ቪቫ ጣይቱ እየተባለ የሚዘገበው።

በተለይም ኢንፎርሜሽን ለማግኘት በሚያስቸግርበት በዚያ ዘመን ታላላቅ ሚዲያዎች ስለ ሚኒሊክና ጣይቱ ሃያልነት፣ ስለ ኢትዮጵያ ህዝቦች የነጻነት ተጋድሎና ጀግንነት በተከታታይነት እንዲዘግቡ ያደረጋቸው ከገለልተኛ ምሁራን ጋር ቀድሞ የተሰራው ስራ ውጤት ነው ሲሉ ይናገራል።

በሚካሄዱ ዓለም አቀፍም ሆነ አህጉር አቀፍ ስምምነቶች ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው እንደዚህ ዓይነት ችግር ውስጥ ላለመግባት ነው። በርግጥ የአድዋ ጦርነት ስምምነት ኖረም አልኖረ፤ ጸደቀም አልጸደቀ፤  ፈረሰም አልፈረሰ… አይቀርም ነበር። አፍሪካን ተቀራምቶ በቅኝ ግዛት ስር ማዋል የበርሊን ኮንፈረንስ ውጤት በመሆኑ።

የአንድ ቃል የትርጉም ልዩነት በዘመኑ ታላቁ የአድዋ ጦርነትን አስከተለ። በጦርነቱም እብሪተኛውና ፋሽስቱ ጣሊያነ ድባቅ ተመታ ። ኢትዮጵያም የዓለም የነጻነት ብርሃን መሆኗን አስመሰከረች። ለጥቁሮች ነጻነትም የጨለማ ቀንዲል በመሆኗ ለዘለዓለም ሲጠቀስ ይኖራል።

በተለይም በወረቀት ተከትቦ የሚቀመጥ ቃል ለወደፊት በህግ ፊት ቀርቦ የመጽናት እድሉ ሰፊ ስለሆነ ጥንቃቄን እንደሚያሻው ማረጋገጫ ነው። ለዛ ነው በተለያዩ ድርድሮች ያገባኛል የሚሉ ሰዎች ሁሉ እንዲሳተፉና በጋራ መግባባት ላይ እንዲደርሱ የሚፈለገው።

በሀገር ጉዳይ የህዳሴውን ግድብ ጨምሮ የሚካሄዱ ስምምነቶች የዛሬውን ትውልድ ወደ እልቂት የማያመሩና የቀጣዩን ትውልድ የመጠቀም መብቱን የማይገድቡ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይገባል መልእክታችን ነው ። መልካም የሰላምና የብልፅግና ዘመን !።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም