በኮንታ ልዩ ወረዳ በደረሰ የመሬት መደርመስ አደጋ የሰዎች ህይወት አለፈ

83
ጅማ ኢዜአ ጥቅምት 3 /2012 በደቡብ ክልል ኮንታ ልዩ ወረዳ በደረሰ የመሬት መደርመስ አደጋ የሰዎች ህይወት ማለፉን የልዩ ወረዳው አስተዳደር አስታወቀ፡፡ የልዩ ወረዳው ምክትል አስተዳደር አቶ ፋንታሁን ብላታ እንደገለጹት አደጋው የደረሰው ጥቅምት 2/2012 ዓ.ም ከለሊቱ አስር ሰዓት ተኩል አካባቢ ነው፡፡ በአደጋውም የስድስት ቤተሰብ አባል የሆኑ  21 ሰዎች በተደረመሰው መሬት አፈር ተጭኗቸው ህይወታቸው ሳያልፍ እንዳልቀረ መገመቱን አመልክተው ከመካከላቸውም13 ሴቶችና ቀሪዎቹ ወንዶች መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ እስካሁን ባለው ሂደትም የአምስት ሰዎች አስክሬን በቁፋሮ መውጣቱንና  የቀሪዎቹን ለማውጣት ህብረተሰቡ  ርብርብ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በልዩ ወረዳው ቀበሌ ሶስት ልዩ ስሙ አመያ በተባለው ስፍራ በሚገኙ መኖሪያ ቤቶች ላይ በደረሰው በዚሁ አደጋ ህይወታቸው ያለፈው ሰዎች ተኝተው ባለቡት ሁኔታ እንደሆነ ተመልክቷል። ዝርዝር መረጃውን የጅማው ሪፖርተራችን እንዳደረሰን  እናቀርባለን።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም