በእንጅባራና በደብረ ብርሃን ከተሞች በእርድ እንስሳት ላይ የዋጋ ጭማሪ ታይቷል

135

ባህር ዳር/ ደብረ ብርሃን ሚያዝያ 19 / 2011በአማራ ክልል በእንጅባራና ደብረ ብርሃን ከተሞች የፋሲካን በዓል ምክንያት በማድረግ በእርድ እንስሳት ላይ የዋጋ ጭማሪ መታየቱን ሸማቾች ተናገሩ።

በእንጅባራ ከተማ ነዋሪ አቶ አዲሱ ደነቀው ለኢዜአ እንደገለጹት በዘንድሮው በዓል የእርድ እንስሳት አቅርቦት ጥሩ ቢሆንም፣ በበግና በፍየል የዋጋ ጭማሪ ታይቷል።

እየተደረገ ባለው ግብይትም በግ ከ1 ሺህ 400 ብር እስከ 5 ሺህ 500 ድረስ እየተሸጠ ነው ብለዋል፡፡

የዚህ ዓመት የፋሲካ በዓል ግብይትም ካለፈው ዓመት የበግ ዋጋ በአማካኝ የአንድ ሺህ ብር ጭማሪ መታየቱን ገልጸዋል፡፡

የዶሮ ዋጋም ዝቅተኛው ከ30 ብር እስከ ከፍተኛው 280 ብር መሸጡን የተናገሩት ደግሞ ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ብርሃኑ ጋሸ ናቸው።

ወይዘሮ እመቤት ስለሺ የተባሉ ነዋሪ በበኩላቸው ከአምስት ቀናት በፊት 13 ብር የነበረው ቀይ ሽንኩርት በዓሉን ምክንያት በማድረግ ወደ 18 ብር ከፍ ማለቱን ገልጸዋል።

የእንጅባራ ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ልዩወርቅ የቆየ በበኩላቸው ለከተማው ነዋሪዎች 263 ኩንታል የዳቦ ዱቄትና 37 ሺህ ሊትር ዘይት ቀርቦ እየተከፋፈለ ነው፡፡

ጽህፈት ቤቱ በተለይ በቂ ምርት እያለ በዓሉን ምክንያተ በማድረግ ያለአግባብ ዋጋ በማናር ለመጠቀም የሚሞክሩ ነጋዴዎች ላይ  ለህግ ለማቅረብ ክትትል እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

በተመሳሳይ በደርብርሃን ከተማ የትንሳኤን በዓል ምክንያት በማድረግ ገበያ በቀረቡ የእርድና ሌሎች ምርቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ እንዳሳዩ ነዋሪዎች አስታውቀዋል፡፡

ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ኃይሉ አበበ እንደተናገሩት የደለበ ሰንጋ ከ14 ሺህ እስከ 32 ሺህ ብር፣

የበግ ሙክትም ከ2 ሺህ 200 ብር እስከ 6ሺህ ብር በመሸጥ ላይ ነው።

ወይዘሮ ዓይናለም ንጉሴ በበኩላቸዉ ቀይ ሽንኩርት በኪሎ 20ብር፣ ነጭ ሽንኩርት በኪሎ ከ60 ብር እስከ 75ብር በመሸጥ ላይ ነው ብለዋል፡፡

ቅቤ በኪሎ ከ270 ብር እስከ 330ብር እየተሸጠ መሆኑንና ካለፈው ዓመትም እስከ 80 ብር ጭማሪ እንዳሳየ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም