የሰብዓዊ መብቶች ትምህርት በትምህርት ስርዓት ውስጥ ሊካተት ነው

283

አዲስ አበባ (ኢዜአ) ጥር 26/2015 የትምህርት ሚኒስቴርና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የሰብዓዊ መብቶች ትምህርትን በመደበኛና መደበኛ ባልሆኑ የትምህርት ሥርዓት ውስጥ ለማካተትና ለማጠናከር የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል።

ስምምነቱን የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል በቀለ ተፈራርመዋል።

May be an image of 9 people and people standing

የስምምነት ሰነዱ የሰብዓዊ መብቶችን ወደ ማህበረሰቡ ከማስረፅ አኳያ ተደራሽነትን በመጨመር ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋልም ተብሏል።

የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ሰላም ሊመጣ የሚችለው ሰብዓዊ መብቶች ሲከበሩ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም መብትና ግዴታውን መለየት የሚችል ማህበረሰብ መፍጠር ይገባል ብለዋል።

በዚህም ረገድ ስምምነቱ ከፍተኛ ድርሻ እንዳለው ገልፀዋል።

የሰብዓዊ መብቶች ትምህርትና ስልጠና ከቅድመ መደበኛ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ድረስ ለመሥጠት እንደሚሠራ በስምምነቱ ተገልጿል ።

ለዚህም ይረዳ ዘንድ የሰብዓዊ መብቶች ትምህርትን በመደበኛው ትምህርት እንደ ግብረ- ገብ እና ዜግነት ትምህርት ውስጥ ትርጉም ባለው መልኩ በማካተት እንዲሠጥ ይደረጋል ተብሏል።


የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) በበኩላቸው ስምምነቱ በኢትዮጵያ ውስጥ ሰብዓዊ መብቶችን ከማስፋፋት አንጻር ጉልህ ሚና አለው ብለዋል።


"የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ለሀገራችን ፈተና ሆኖ ቆይቷል ያሉት ኮሚሽነሩ ይህንንም ለመግታት ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር የምንሰራው ስራ ወሳኝ ነው" ብለዋል።


የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንም የሙያ እገዛ ከመሥጠት ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎች እንደሚደረጉ መገለጹን ከትምህርት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም