በቻን ውድድር ዛሬ የምድብ ጨዋታዎች ፍጻሜያቸውን ያገኛሉ

168

አዲስ አበባ (ኢዜአ) ጥር 16/2015 በአልጄሪያ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው ሰባተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና(ቻን) ዛሬ የምድብ ጨዋታዎች ይጠናቀቃሉ።

በጫወታዎቹም ሩብ ፍጻሜ የሚገቡ ሁለት ቀሪ አገራት ይለዩበታል።

12ኛ ቀኑን በያዘው የቻን ውድድር ዛሬ በምድብ አራት በሚሉድ ሀዴፊ ስታዲየም ከምሽቱ 1 ሰአት ማሊ ከሞሪታኒያ ይጫወታሉ።

ሶስት አገራት በሚገኙበት ምድብ ሁለቱ አገራት ተመሳሳይ አንድ ነጥብ ይዘው ማሊ ብዙ ባገባ በሚለው ሕግ በልጣ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።

አንድ አገር ብቻ ወደ ሩብ ፍጻሜው በሚያልፍበት ምድብ ከማሊ ወይም ከሞሪታኒያ ያሸነፈው አገር ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፉን ያረጋግጣል።

ጨዋታው በአቻ ውጤት ከተጠናቀቀ በእግር ኳስ ሂሳባዊ ስሌት የተሻለ ውጤት ያለው አገር ወደ ሩብ ፍጻሜው ያልፋል።

በምድቡ ሁለት ጨዋታዎችን ያደረገችው አንጎላ በሁለት ነጥብ እየመራች ነው።

በተያያዘም በምድብ አምስት ከምሽቱ 4 ሰአት ካሜሮን ከኒጀር በሚሉድ ሀዴፊ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።

ምድቡን በሶስት ነጥብ የምትመራው ካሜሮን ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት ወደ ሩብ ፍጻሜው ያስገባታል።

በአንጻሩ ኒጀር ማሸነፍ ብቻ ነው ወደ ሩብ ፍጻሜው የሚያሳልፋት።

ምናልባት የ'一 te TotalEnergies AFRICAN NATIONS CHAMPIONSHIP ALGERIA 2022 GROUP C w D L GD PTS MADAGASCAR 3 3 0 7 GHANA 9 32014 4 3 2 0 1 6 SUDAN 3102-23 #TotalEnergiesCHAN2022' የሚል ጽሑፍ ምስል

በሌላ በኩል ትናንት በቻን ውድድር በምድብ ሶስት በተደረገ ጨዋታ ማዳጋስካር ሱዳንን 3 ለ 0 አሸንፋለች።

ውጤቱንም ተከትሎ ማዳጋስካር በዘጠኝ ነጥብ ምድቧን በመሪነት በማጠናቀቅ ወደ ሩብ ፍጻሜው አልፋለች።

በምድቡ ጋና በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅላለች።

በዚህ ምድብ ሞሮኮ ራሷን ከውድድሩ ማግለሏን ተከትሎ ማዳጋስካር፣ጋና እና ሱዳን የ3 ለ 0 እና የ3 ነጥብ ፎርፌ ውጤት ማግኘታቸው ይታወቃል።

በቻን ውድድር የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ጥር 19 እና 20 2015 ዓ.ም ይካሄዳሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም