በዓለም ዋንጫው ዴንማርክ ከፈረንሳይ እና ቱኒዚያ ከአውስትራሊያ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው

143

አዲስ አበባ (ኢዜአ) ሕዳር 17 ቀን 2015 በኳታር አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ዛሬ ዴንማርክ ከፈረንሳይ እና ቱኒዚያ ከአውስትራሊያ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል።

በኳታር አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው ዓለም ዋንጫ ዛሬ ሰባተኛ ቀኑን ይዟል።

የምድብ ሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች ትናንት የተጀመሩ ሲሆን ዛሬም አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ።

በምድብ አራት አፍሪካዊቷ አገር ቱኒዚያ ከአውስትራሊያ በአል ጃኑብ ስታዲየም ከቀኑ 7 ሰአት ጨዋታቸውን ይደርጋሉ።

ቱኒዚያ በመጀመሪያ ጨዋታዋ ከዴንማርክ ያለ ምንም ግብ አቻ ስትለያይ አውስትራሊያ በፈረንሳይ 4 ለ 1 መሸነፏ የሚታወስ ነው።

በምድብ ሶስት በኢጁኬሽን ሲቲ ስታዲየም ሳዑዲ አረቢያ ከፖላንድ ከቀኑ 10 ሰአት ይጫወታሉ።

ሳዑዲ አረቢያ በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ አርጀንቲናን 2 ለ 1 በማሸነፍ ያልተጠበቀ ውጤት ማስመዝገቧ ይታወቃል።

በአንጻሩ ፖላንድ ከሜክሲኮ ጋር ባደረገችው ጨዋታ ያል ምንም ግብ አቻ ተለያይታለች።

በምድብ አራት የ21ኛው ዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ፈረንሳይ በስታዲየም 974 ከዴንማርክ ጋር ከምሽቱ 1 ሰአት የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል።

80 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግደው ሉሳይል ስታዲየም በምድብ ሶስት በመጀመሪያ ጨዋታዋ ያልተጠበቀ ሽንፈት ያስተናገደችው አርጀንቲና ከሜክሲኮ ከምሽቱ 4 ሰአት ትጫወታለች።

ሕዳር 11 ቀን 2015 ዓ.ም የተጀመረው 22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ እስከ ታህሳስ 9 ቀን 2015 ዓ.ም ይቆያል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም