ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ - ኢዜአ አማርኛ
ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ

መስከረም 25 /2015 (ኢዜአ) የ2015 ዓ.ም ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት መርሐግብር ዛሬ በሚደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ይጀመራል።
በባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም ባህር ዳር ከተማ ከወልቂጤ ከተማ ከቀኑ 7 ሰአት፤ አርባምንጭ ከተማ ከኢትዮጵያ መድን 10 ሰአት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ነገ ኢትዮ ኤሌትሪክ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀኑ ሰባት እንዲሁም ለገጣፎ ለገዳዲ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 10 ሰአት ይጫወታሉ።

በሁለተኛ ሳምንት ፋሲል ከነማ ከወላይታ ድቻ ሊያደርጉት የነበረው የሊጉ ጨዋታ አፄዎቹ እሁድ መስከረም 29 ቀን 2015 ዓ.ም በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ከቱኒዚያው ሰፋክሲያን ባለባቸው የማጣሪያ ጨዋታ ምክንያት መርሐግብሩ ሕዳር 27 ቀን 2015 ዓ.ም በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሜዳ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
ፋሲል ከነማ ከቱኒዚያው ክለብ ጋር ያለበትን ጨዋታን ታሳቢ በማድረግ በሶስተኛ ሳምንት ከባህር ዳር ጋር ከተማ ሊያደርገው የነበረው ጨዋታ ጥቅምት 19 ቀን 2015 ዓ.ም በባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም እንደሚደረግ ገልጿል።
አፄዎቹ በአፍሪካ መድረክ ባለበት ጨዋታ ምክንያት በሁለተኛና ሶስተኛ ሳምንት የሊጉ ጨዋታዎች ላይ መጠነኛ ማሻሻያ መደረጉን አመልክቷል።
የሁለተኛ ሳምንት የሊጉ መርሐግብር እስከ መስከረም 30 ቀን 2015 ዓ.ም ይቆያል።
የዘንድሮው ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ዙር መርሐ ግብሮች በባህር ዳር ስታዲየም(ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ሳምንት)፣በድሬዳዋ ስታዲየም (ከስድስተኛ እስከ 10ኛ ሳምንት) እንዲሁም በአዳማ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩንቨርስቲ ሜዳ(ከ11ኛ እስከ 15ኛ ሳምንት) ይከናወናሉ።