የኢሬቻ በዓል በሰላም ተጠናቋል- ግብረ-ኃይሉ - ኢዜአ አማርኛ
የኢሬቻ በዓል በሰላም ተጠናቋል- ግብረ-ኃይሉ

መስከረም 22 ቀን 2015 (ኢዜአ) የኢሬቻ በዓል በሰላም መጠናቀቁን የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ-ኃይል አስታወቀ።
በአዲስ አበባና በቢሾፍቱ ከተማ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተሳታፊዎች የታደሙበት የሆራ-ፊንፊኔና የሆራ-ሀርሰዴ ኢሬቻ በዓል በሰላም መጠናቀቁን ግብረ-ኃይሉ አስታውቋል።
ግብረ-ኃይሉ በዓሉ ሰላማዊ ሆኖ እንዲከበር ከዋዜማው ጀምሮ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቅድመ መከላከል ስራን ከህዝቡ፣ ከኦሮሞ አባ ገዳዎች ህብረትና ከበዓሉ አዘጋጅ ኮሚቴዎች ጋር ተቀናጅቶ ሲሰራ መቆየቱ ተገልጿል፡፡
በዓሉ በሰላም እንዲጠናቀቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረገው ህዝብ፣ ለኦሮሞ አባ ገዳዎች ህብረትና ለበዓሉ አስተባባሪ ኮሚቴዎች እንዲሁም የፀጥታና ደህንነት ኃይሎች ምስጋና አቅርቧል፡፡
የሀገራችን ጠላቶችና እነርሱ የሚመሯቸው አሸባሪዎች ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በደህንነታችን ላይ አደጋ ለማድረስ ስለሚጥሩ ህብረተሰቡ አካባቢውን ነቅቶ እንዲጠብቅም ግብረ-ኃይሉ ጥሪ አቅርቧል።
ቀጣይ በሀገራችን የሚከበሩ ሌሎች ህዝባዊና ሐይማኖታዊ በዓላት ላይ ህብረተሰቡ እስካሁን እያሳየ ያለውን ቀና ትብብር አጠናክሮ እንዲቀጥልም የጋራ ግብረ- ኃይሉ ጠይቋል፡፡