መገናኛ ብዙኃን ስለ አገራዊ ምክክሩ ምንነትና የውይይት ጽንሰ ዐሳብ በተለያዩ ቋንቋዎች ግንዛቤ እንዲፈጥሩ ተጠየቀ - ኢዜአ አማርኛ
መገናኛ ብዙኃን ስለ አገራዊ ምክክሩ ምንነትና የውይይት ጽንሰ ዐሳብ በተለያዩ ቋንቋዎች ግንዛቤ እንዲፈጥሩ ተጠየቀ
መስከረም 12 ቀን 2015 (ኢዜአ) መገናኛ ብዙሃን ስለ አገራዊ ምክክሩ ምንነትና የውይይት ጽንሰ ዐሳብ በተለያዩ ቋንቋዎች ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በመፍጠር ሚናቸውን እንዲወጡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጠየቀ።
ኮሚሽኑ የሚዲያና ኮሚኒኬሽን ዘርፍ ስትራቴጂክ ረቂቅ ዕቅዱ ላይ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ውይይት እያደረገ ነው።
በዚሁ ጊዜ ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ እንዳሉት መገናኛ ብዙሀን ለአገራዊ ምክክሩ መሳካት ወሳኝ ሚና አላቸው።
የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሚቀጥሉት ጊዜያት ከህዝብ ጋር በየደረጃው መድረስ ይጠበቅበታል ብለዋል።
ለዚህም መገናኛ ብዙሀን በተለያዩ ቋንቋዎች የኮሚሽኑን ምንነት፣ የውይይቱን ጽንሰ ሀሳብ፣ የውይይቱን ሂደት፣ አጀንዳ አሰባሰብን፣ የተሳታፊዎችን ልየታና ሌሎች የምክክሩን ሂደት ለህዝብ ማድረስ ይገባቸዋል ብለዋል።
የተዘጋጀው ረቂቅ የሚዲያና ኮሚኒኬሽን ዘርፍ ስትራቴጂክ ዕቅድም ለመረጃ ተጀራሽነትና መገናኛ ብዙሃን ጋር አብሮ ለመስራት እንዲረዳ ተደርጎ መሰናዳቱን ነው የገለጹት።
በውይይቱ የኮሚሽኑ ኮሚኒኬሽን ዘርፍ ስትራቴጅክ ረቂቅ ዕቅድ ቀርቦ ውይይት የተደረገ ሲሆን ምሁራን፣ የመገናኛ ብዙሃን ተቋማት ተወካዮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተው በረቂቅ ስትራቴጂው ላይ ግብአት ሰጥተዋል።
የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሚያከናውናቸው ተግባራት ዙርያ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ይታወቃል።