በጋሞ ዞን ከ104 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ የንፁህ መጠጥ ውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች ተመረቁ

248

ነሐሴ 8 ቀን 2014 (ኢዜአ)በጋሞ ዞን ከ104 ሚሊዮን ብር ወጪ ግንባታቸው የተጠናቀቁ 16 የንጹህ የመጠጥ ውሃና የመስኖ ፕሮጀክቶች በዛሬው ዕለት ተመረቁ፡፡

ለምረቃ ከበቁት 16 ፕሮጀክቶች መካከል 9ኙ የንጹህ የመጠጥ ውሃ ሲሆኑ 7ቱ ደግሞ የመስኖ ፕሮጀክቶች ናቸው፡፡

ፕሮጀክቶቹ የተገነቡት በአርባምንጭ ከተማና በዙሪያዋ፣በዲታ፣በገረሰ ፣በካምባ ፣በቦንኬ፣ በዳራማሎ፣ በቁጫ፣ በጋርዳ ማርታና በቆጎታ ወረዳዎች መሆኑ ተገልጿል፡፡

የንጹህ መጠጥ ውሃ ተቋማቱ ከ46 ሺህ በላይ እንዲሁም የመስኖ ፕሮጀክቶቹ ከ3 ሺህ በላይ የአካባቢው ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡

በምረቃ ስነስርአቱ ላይ የደቡብ ክልል ውሃ፣መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር አክሊሉ አዳኝና በደቡብ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ ዶክተር አበባየሁ ታደሰን ጨምሮ ሌሎች የክልልና የጋሞ ዞን የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ ባለሙያዎችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም