ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው የሕግ ማስከበር እርምጃው ተጠናክሮ እንዲቀጥል አቅጣጫ አስቀመጠ

71

ሰኔ 15 ቀን 2014 (ኢዜአ) የብልጽግና ፓርቲ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የሕግ ማስከበር እርምጃው ተጠናክሮ እንዲቀጥል አቅጣጫ አስቀመጠ፡፡

የብልጽግና ፓርቲ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባውን እያካሄደ ነው።

ኮሚቴው በስብሰባው በወቅታዊ ሀገራዊ የጸጥታ ጉዳይ እና እየተወሰደ ባለው የሕግ ማስከበር እርምጃ ላይ ተወያይቷል።

በዚህም አሸባሪ ቡድኖች በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በንጹሃን ላይ የፈጸሟቸውን ግድያዎች አውግዟል።

የሽብር ቡድኖቹ ይህን የቀቢጸ ተስፋ ጥቃት እየፈጸሙ ያሉት እየተወሰደባቸው ባለው ጠንካራ የህግ ማስከበር እርምጃ የደረሰባቸውን ኪሳራ ለመሸሸግ መሆኑን ኮሚቴው ገምግሟል።

ሽብርተኞችን የመደምሰስ የሕግ ማስከበር እርምጃው ከዚህ ቀደም የጸጥታው ምክር ቤት ባሳለፈው ውሳኔ መሰረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አቅጣጫ አስቀምጧል።

በአሁኑ ሰዓት ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በተዛማጅ እና ሌሎች ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እየተወያየ እንደሚገኝ ከፓርቲው የፌስቡክ ገጽ ላይ የተገኘው መረጃ ያሳያል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም