በተያዘው ክረምት በኦሮሚያ ክልል ስድስት ሺህ የቅድመ-መደበኛ ትምህርት ቤቶች ይገነባሉ-የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ

156

ሰኔ 03 ቀን 2014 (ኢዜአ) በተያዘው ክረምት በኦሮሚያ ክልል ስድስት ሺህ የቅድመ-መደበኛ ትምህርት ቤቶች እንደሚገነቡ የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ አስታወቀ።

በምስራቅ ሸዋ ዞን ቦራ ወረዳ ማሊሞ ቀበሌና በምዕራብ አርሲ ዞን ዶዶላ ከተማ የትምህርት ቤቶቹ ግንባታ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ተካሄዷል።

በ’ቡኡራ ቦሩ’(የነገ ተስፋ) የመማሪያ ክፍሎች ግንባታና የመምህራን ስልጠና ስራዎች ለሚገነቡት ስድስት ሺህ ትምህርት ቤቶች እስከ 30 ቢሊዮን ብር ወጪ እንደሚያስፈልግ ተገልጿል።

የግንባታው ወጪ በዜግነት አገልግሎት በሚሳተፉ በጎ ፈቃደኞች፣ ባለሃብቶች፣ በጎ አድራጊ ተቋማትና በውጭ ከሚኖሩ ዳያስፖራዎች እንደሚሸፈን የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ቶላ በሪሶ ገልጸዋል።

ትምህርት ቤቶቹ በ2015 ዓ.ም የትምህርት ዘመን እድሜያቸው አምስት ዓመት የሆናቸውን ሕጻናት እንደሚቀበል ተናግረዋል።

የግንባታው አላማ በክልሉ የገጠር ክፍሎች ያሉ ዜጎች የትምህርት ተደራሽነት ማስፋት መሆኑን አመልክተዋል።

በ2013 ዓ.ም ክረምት በጎ ፈቃደኞችን በማስተባበር 3 ሺህ 11 የቅድመ-መደበኛ ትምህርት ቤቶች መገንባታቸውንና 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ተማሪዎች ተቀብለው እያስተማሩ ይገኛሉ ነው ያሉት ዶክተር ቶላ።

በ2015 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ የቅድመ-መደበኛ ትምህርት ቤቶችን ወደ 12 ሺህ ከፍ ለማድረግ መታቀዱን ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም