አመራሩ ሁለንተናዊ አቅሙን በማሳደግ የህዝብ አገልግሎት እርካታን ለማረጋገጥ መስራት ይጠበቅበታል--አቶ ግርማ የሺጥላ

ባህር ዳር ሰኔ 1/2014 (ኢዜአ)በየደረጃው ያለው የክልሉ አመራር እራሱን በማብቃት የህዝብ አገልግሎት እርካታን ለማረጋገጥ መትጋት እንደሚጠበቅበት በአማራ ክልል የብልፅግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ አስታወቁ።

''አዲስ ፖለቲካዊ ዕይታ፣ አዲስ ሀገራዊ እምርታ'' በሚል መሪ ሀሳብ የከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ስልጠና መክፈቻ ዛሬ ማምሻውን በባህር ዳር ከተማ ተካሂዷል።

የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ   እንደገለጹት በየደረጃው ያለው የክልሉ አመራር  የተሰጠውን ሃላፊነት በአግባቡ በመፈጸም የህዝቡን የአገልግሎት ጥያቄዎች ለመመለስ  መትጋት  ይጠበቅበታል።

የሚሰጠውስልጠና  በእውቀት፣ በክህሎትና በአስተሳሰብ ብቃት ያለው ጠንካራ አመራር በመገንባት የህዝብ አገልግሎት እርካታን ማረጋገጥን አላማ  ያደረገ  ነው ብለዋል።

በየደረጃው ያለው ከፍተኛና መካከለኛ አመራር የተሰጠውን መንግስታዊና ህዝባዊ ኃላፊነት በብቃት መወጣት እንዲችል አቅሙን በስልጠና መገንባት አስፈላጊ ሆነ መገኘቱን አመላክተዋል።

ብቃት ያለው አመራር ለመፍጠር ታስቦ የተዘጋጀውን ስልጠና ተሳታፊው አመራር  በትጋት መከታተል እንዳለበት አሳስበዋል።

እስከ ሰኔ 7/2014 በሚቆየው ስልጠና ከ2 ሺህ በላይ የክልሉ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች እንደሚሳተፉ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም