የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት ከ7 ሺህ በላይ መጻሕፍት አበረከተ - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት ከ7 ሺህ በላይ መጻሕፍት አበረከተ

ግንቦት 25/2014 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ከተለያዩ ቤተ-እምነቶች ያሰባሰባቸውን ከ7 ሺህ በላይ መጻሕፍትን ለአብርሆት ቤተ-መጽሐፍት አበረከተ።
ለአብርሆት ቤተ-መጽሐፍት "ሚሊዮን መጻሕፍት ለሚሊኒየሙ ትውልድ" በሚል መሪ ኃሳብ ለአንድ ወር መጻሕፍትን ለማሰባሰብ የቀረበውን ጥሪ ተከትሎ በርካታ ተቋማትና ግለሰቦች ምላሽ እየሰጡ ነው።
ይህንንም ተከትሎ የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ከተለያዩ ቤተ-እምነቶች ያሰባሰባቸውን ከ7 ሺህ በላይ መጻሕፍት ለቤተ-መጽሐፍቱ በዛሬው ዕለት አስረክቧል።
የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ጸሐፊ ቀሲስ ታጋይ ታደለ፤ መጻሕፍቱ ከሰባት ቤተ-እምነቶችና ከአማኞቻቸው የተሰባሰቡ መሆናቸውን በመጥቀስ ለቤተ-መጽሐፍቱ አስረክበዋል።
መጻሕፍቱ ኃይማኖታዊ ይዘት ያላቸው፣ የፍልስፍና፣ የአስተዳደር፣ በሰላም ግንባታና በአብሮነት ላይ ትኩረት ያደረጉ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል።
ጉባኤው አሁን ላይ ከ7 ሺህ በላይ ያሰባሰባቸውን መጻሕፍት ማስረከባቸውን ጠቁመዋል።
በቀጣይም ጉባኤው ከሰባቱ ቤተ-እምነቶች ጋር በመተባበር በርካታ ቁጥር ያላቸው መጻሕፍትን አሰባስቦ ለማስረከብ ማቀዱን ጠቅሰው፤ ቤተ-እምነቶችም መጻሕፍት እንዲያሰባስቡ ጥሪ አቅርበዋል።
የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽህፈት ቤትን ወክለው መጻሕፍቱን የተረከቡት ዶክተር ታምራት ኃይሌ፤ ጉባኤው ለአብርሆት ቤተ-መጽሐፍት ላደረገው ድጋፍ አመስግነዋል።
"ቤተ-እምነቶች የእውቀት ማምረቻ፤ የእውቀት ማስተላለፊያ ናቸው።" ያሉት ዶክተር ታምራት በቀጣይ ለማሰባሰብ ያቀዷቸውን መጻሕፍት እንዲያሳኩም አበረታተዋል።
በርካታ ተቋማት ለአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት የመጻሕፍት ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ጠቁመው፤ አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል።
የመገናኛ ብዙኃንም ለቤተ-መጽሐፍቱ የሕዝብ ድጋፍ እንዳይለይ እያደረጉ ላለው አስተዋጽኦ አመስግነዋል።