የኢትዮጵያ አየር መንገድ የጥገና ማዕከሉን ዲጂታላይዝ አደረገ

225

ግንቦት 17/2014/ኢዜአ/ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአውሮፕላን ጥገና ማዕከሉን ''ሀንጋር'' ዲጂታላይዝ ማድረጉን ገለጸ።

የጥገና ማዕከሉ ወደ ዲጂታል መቀየሩ አየር መንገዱ በየአመቱ ለወረቀትና የሰው ሃይል ያወጣው የነበረውን 500 ሚሊዮን ብር ያስቀራል ተብሏል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው፤ እንደገለጹት የአየር መንገዱን የአውሮፕላን ጥገና ማዕከል ዲጂታል ለማድረግ የአራት አመት ፕሮጀክት ቀርጾ ሲሰራ ቆይቷል ብለዋል።

የጥገና ማዕከሉ አስካሁን በወረቀት የታገዘ አሰራር እንደነበረው ጠቅሰው አሁን ላይ ሙሉ ለሙሉ ዲጅታላይዝ ወደ ሆነ አስራር መሸጋገሩን ገልጸዋል።

አዲሱ አሰራር አውሮፕላኖች ከድርጅቱ ሲወጡ፣ የተከራዩ ከሆነም ሲመለሱ ወይም በሌላ መንገድ ሲተላለፉ ሪከርድን ለማስተካከል የሚባክነውን ጊዜ ያስቀረ ስለመሆኑም አብራርተዋል።

የጥገና ማዕከሉን በአውሮፓና ሌሎች የዓለም አገራት ከሚሰጡ አገልግሎቶች ጋር ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችሉ አሰራሮች ይዘረጋሉ ብለዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የኦፕሬሽን ዘርፍ ሃላፊ ረታ መላኩ፤ የጥገና ማዕከሉ ዲጅታላይዝ መሆን ለአሰራር ፍጥነትና ቅልጥፍና የጎላ ሚና ያለው መሆኑን ገልጸዋል።         

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም