ሚኒስቴሩ ከተቋማት ያሰባሰበውን ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ የዓይነትና የገንዘብ ድጋፍ አስረከበ

ሚያዝያ 16 ቀን 2014 (ኢዜአ) የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፌደራል ጉምሩክ ኮሚሽንና ብልጽግና ፓርቲ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ያሰባሰበውን ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የዓይነትና የገንዘብ ድጋፍ አስረከበ።

ሚኒስቴሩ የትንሳዔ በዓልንና የረመዳን ጾምን ምክንያት በማድረግ በተለያዩ ምግባረ ሰናይ ማዕከላት ተጠልለው ለሚገኙ አረጋውያን፤ አቅመ ደካሞች፤ አካል ጉዳተኞች እና የአእምሮ ሕሙማን ነው ድጋፉን ያደረገው።

በድጋፍ መርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ የሀገር ባለውለታ የሆኑ አረጋውያን፤ ጧሪና ጠያቂ ያጡ፤ የአእምሮ ሕሙማንና አካል ጉዳተኞችን በአጠቃላይ በተለያየ ችግር ውስጥ ያሉ ወገኖችን መደገፍና የሚፈልጉትን ጤናማ ሕይወት እንዲኖሩ ማስቻል የሁላችንም ግዴታ ነው ብለዋል።

ጉብኝቱ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬና ሚኒስትር ዴኤታዎች እንዲሁም የኢፌዴሪ ጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታና ሌሎች የስራ ኃላፊዎች ጋር በመቀናጀት የተከናወነ መሆኑን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም